በመዲናዋ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በተለምዶ ሿሿ የሚባለዉን የማታለል ወንጀሎች ሲፈፅሙ የነበሩ 21 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸዉን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በለሚ ኩራ፣ በቂርቆስና በአራዳ ክፍለ ከተሞች የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ በመምሰል የተለያዩ ወንጀሎችን ሲፈጽሙ የነበሩ ሲሆን ከህብረተሰቡ በተሰጠ ጥቆማ በአጠቃላይ 21 ተከሳሾች ለዚሁ ወንጀል ተግባር ሲጠቀሙባቸው ከነበሩባቸው ሦስት ተሽከርካሪዎች ጋር በፒያሳ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ በቁጥጥር ስር መዋላቸዉን የከተማዋ ፖሊስ ለአዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ በላከዉ መረጃ አስታውቋል፡፡
ሃያ አንዱም ተጠርጣሪዎች በተለያዩ ጊዜአት ተሽከርካሪዎችን በመጠቀም ጭምር ወንጀል ሲፈጽሙ እንደነበር ተገልጿል፡፡
ወንጀል ፈጻሚዎች ወቅቱ ክረምትና የዝናብ ወቅት መሆኑን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ወንጀል ሲፈጽሙ የነበረ ሲሆን የትራንስፖርት ተጠቃሚዎችም ከዝናብ ለመሸሽና ፈጥኖ ትራንስፖርት ለማግኘት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ለወንጀል ተጋላጭ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባቸዉ ፖሊስ አስታዉቋል፡፡