አዲስ አበባ ዓመቱን በሙሉ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሚናዋን አጠናክራ ትቀጥላለች ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዛሬው እለት ከተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር በአንድ ጀንበር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አሻራቸውን አሳርፈዋል።
በዚሁ ጊዜ ኢትዮጵያ ባለፉት ስድስት ዓመታት ምድርን አረንጓዴ የማልበስ አስደናቂ ስራ ሰርታለች ብለዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በነቂስ ወጥቶ ለአንድ ዓላማ የሚሰለፍበት የጋራ አጀንዳ መሆኑንም ነው ያነሱት።
ይህ ተግባር ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በጽኑ መሰረት ላይ የሚያንጽ መሆኑንም አንስተዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል የምታደርገውን ጥረት በመደገፍ ረገድም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው የገለጹት ከንቲባ አዳነች፤ የሚተከሉ ችግኞች ከውበት ባሻገር ለምግብነት የሚውሉ መሆናቸውን አንስተዋል።
እንደ ከንቲባዋ ገለጻ፣ አዲስ አበባ ዓመቱን ሙሉ በተለያዩ ፕሮግራሞች ችግኞችን በመትከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሚናዋን አጠናክራ እንደምትቀጥል ተናግርዋል።
በዚህም የከተማዋ የደን ሽፋን አሁን ላይ 22 በመቶ መድረሱንና በቀጣዩ ዓመት 30 በመቶ ለማድረስ መታቀዱን አመልክተዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ ”በመትከል ማንሰራራት” በሚል መሪ ሀሳብ 700 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል የተያዘው ግብ እንዲሳካ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ዐሻራቸውን እያኖሩ ይገኛሉ።