የሚያጋጥሙ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሰላምንና አንድነትን የማጽናት ጥረት የሁላችንም ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ሲሉ የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የበላይ ጠባቂ አባቶችና ተወካዮች አስገነዘቡ።
አራተኛው የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ሀገር አቀፍ የሰላም ኮንፍረንስ የኃይማኖት ተቋማት የበላይ ጠባቂ አባቶችና ተወካዮች የሰላም መልዕክትና ጥሪ በማስተላለፍ ተጠናቋል።
በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ የሃይማኖት ተቋማት የበላይ ጠባቂ አባቶችና ተወካዮች ባስተላለፉት የሰላም መልዕክትና ጥሪ “ሰላምን የማስፈን ስራን አጠናክረን እንቀጥላለን” ብለዋል።
በየትኛውም አጋጣሚ የሚፈጠሩ አለመግባባቶችና ግጭቶች በውይይት እንዲፈቱና ሰላምን በማጽናት የላቀ ሚናቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውንም አረጋግጠዋል።
በኢትዮጵያ ሁሉም አካባቢዎች ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲጎለብት ሁሉም የበኩሉን መወጣት እንዳለበት አንስተው የሚያጋጥሙ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሰላምንና አንድነትን ለማጽናት ሁሉም ሊዘጋጅ እንደሚገባም አፅንኦት መስጠታቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምስተኛውን የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሚያዘጋጅ መሆኑም ታውቋል።