‎የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ በጋራ ለመስራት ተስማሙ

You are currently viewing ‎የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ በጋራ ለመስራት ተስማሙ

AMN – ሐምሌ 30/2017 ዓ.ም

‎የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ብሄራዊ ጥቅም እና በሰላም ጉዳይ ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችል “የቢሾፍቱ ቃል ኪዳን” ስምምነት አድርገዋል።

‎በቢሾፍቱ ሲካሄድ የቆየው ይህ ኮንፍረንስ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ሰላም በማፅናት የፖለቲካ ፓርቲዎች ሚና በሚል መሪ ቃል ሲያካሂድ መቆየቱ ይታወሳል።

‎የቃል ኪዳን ስምምነቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለአገራዊ መግባባት፣ ብሄራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ እና የሰለጠነ የፖለቲካ ስነ ምህዳር የማስፋት ይዘት ያለው ስምምነት መሆኑን ከኤ ኤም ኤን ጋር ቆይታ ያደረጉ የፖለቲካ ፖርቲዎች ተናግረዋል።

‎የቦሮ የዴሞክራሲ ፖርቲ ስራ አስፈፃሚ መብራቱ አለሙ ዶ/ር፣ የቃል ኪዳን ስምምነቱ የሰላም ምንነቶችና መገለጫዎች የግንዛቤ ሀሳብ የተወሰደበት እንደሆነ ተናግረዋል።

‎የሰነዱ መዘጋጀት ዋነኛ አላማ በተለያዩ አካባቢዎች እየተከሰቱ ያሉ ግጭቶች እንደሆኑ ጠቁመው፣ እነዚህን ችግሮች የፖለቲካ ፖርቲዎች ሚናቸውን ተወጥተው በሰላማዊ መንገድ ችግሮች እንደሚፈቱ ለማስመዝገብ እንደሆነ ስራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።

‎ፖለቲካ ማለት ግጭቶችን በውይይት፣ በምክክር፣ በሽምግልና መፍታት ማለት ነው ያሉት የፖርቲው ስራ አስፈፃሚ፣ በሰላሚዊ መንገድ ችግሮችን ለመቅረፍ ስምምነቱ ያግዛል ብለዋል።

‎የዴሞክራሲ ባህልና እሴቶች እንዲዳብሩ የቃል ኪዳን ስምምነቱ እንደሚያግዝ፣ ልዩነቶችና ችግሮችን በጠረንጴዛ ዙሪያ ለመፍታት እንደነዚህ ያሉ መድረኮች የነበረውን እሳቤ የሚቀይሩ መሆናቸውም ተገልጿ፡፡

‎በአገራዊ እና ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ የፖለቲካዊ ልዩነቶችን ወደ ጎን በመተው ለጋራ መሰለፍ ሌላኛው የቃልኪዳኑ ስምምነት አንኳር ጉዳይ መሆኑም ተመላክቷል።

‎የአዲስ ትውልድ ፖርቲ ፕሬዝዳንት አቶ ሰለሞን ታፈሰ በበኩላቸው፣ ቃልኪዳኑ እያንዳንዱ የፖርቲ አባል በሚኖርበት አከባቢ ሰላም የማስፈን አስተዋፅኦቸውን እንዲወጡ የሚያደርግ ነው ብለዋል።

‎ከመንግስት ጋር አንድ የሚያደርጋቸውን ጉዳዮች በሶስት የከፈሉት አቶ ሰለሞን፣ የአገር ጉዳይ፣ የሰላም ጉዳይ፣ በአገሪቱ የሚሰሩ መሰረተ ልማቶች የጋራ መሆናቸውን ይገልፃሉ።

‎ሐምሌ 17 ቀን 2017 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ የተከናወነው የቢሾፍቱ ቃል ኪዳን ስምምነት ሰባት አንቀፆችን በውስጥ ያካተተ ስምምነት ነው።

‎ከእነዚህ ስምምነቶች ውስጥ ለብሄራዊ ጥቅምና ለዴሞክራሲ ስረዓት የማፅናት፣የግልፀኝነትና የተጠያቂነት መርህ የማዳበር፣ የግጭት አያያዝና የሰላም ግንባታ ውጤታማነት የመስራት፣ ለአካታችነት፣ ለአገራዊ መግባባትና ብሄራዊ ጥቅም አብሮ የመቆም የሚሉት ጉዳዮች ይገኙበታል።

‎በሔለን ተስፋዬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review