የቀዳማዊት እመቤት ጽ/ቤት አዲስ አበባ ከተማ ለሚገኘዉ ለብርሃን የአይነስውራን አዳሪ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የትምህርትና የህክምና ግብአቶች በስጦታ አበርክቷል።
ጽ/ቤቱ በትምህርት ዘረፍ ላይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ላለፉት አምስት አመታት 35 ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶችን በመላው የሃገሪቱ ክፍሎች ገንብቶ በርካታ ተማሪዎች የትምህርት አገልግሎት እንዲያገኙ አድርጓል፡፡
የጥራት ደረጃቸዉን ጠብቆ ከገነባቸው እጅግ ዘመናዊ ት/ቤቶች ውስጥ አንዱ አዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው ብርሀን የአይነስውራን አዳሪ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ሲሆን ት/ቤቱ ከ400 በላይ የሆኑ ተማሪዎችን ከመላው የሃገሪቱ ክፍሎች ተቀብሎ በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡
ጽ/ቤቱ የትምህርት ቤቱን የመማር-ማስተማር ሂደት እና የት/ቤቱን እና የተማሪዎቹን ፍላጎት በቅርብ ክትትል በማድረግ በርካታ ተጨማሪ ድጋፎችን በማድረግ ላይ ይገኛል።
በዛሬው እለትም የመማር-ማስተማር ሂደቱን ሊያቀላጥፉ የሚችሉ የብሬል ፕሪንተር(ኢምቦሰር) ፣ዲጂታል ሪከርድስ እና በት/ቤቱ ውስጥ ለተማሪዎች አገልግሎት በመስጠት ላይ ለሚገኘው ክሊኒክ የተለያዩ የሕክምና መሳሪያዎች እና መመርመሪያ ሪኤጀንቶችን በስጦታ ማበርከቱን ከጽ/ቤቱ ያገኘነዉ መረጃ ያመላክታል።