ከመስከረም ወር ጀምሮ ከ3.3 ሚሊዮን ለሚበልጡ የመንግስት ሰራተኞች የደመወዝ ማሻሻያ ተግባራዊ ይደረጋል

You are currently viewing ከመስከረም ወር ጀምሮ ከ3.3 ሚሊዮን ለሚበልጡ የመንግስት ሰራተኞች የደመወዝ ማሻሻያ ተግባራዊ ይደረጋል

AMN ነሐሴ 12/2017

ከሶስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ለሚበልጡ የመንግስት ሰራተኞች የደመወዝ ማሻሻያ ለማድረግ ተጨማሪ 160 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግና ይህም የመንግስትን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተገለጸ፡፡

ለመንግስት ሰራተኞች ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ የደመወዝ ማሻሻያ መደረጉ ተመላክቷል።

የገንዘብ ሚኒስቴር የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርምን ወደ ሙሉ ትግበራ ማስገባቱን ተከትሎ ከሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ዕውቅና ተሰጥቶታል።

የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በዕውቅና ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለፁት፥ መንግስት ባለፉት ጥቂት ዓመታት ያካሄዳቸው ዘርፈ ብዙ ሪፎርሞች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል።

በተለይም የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደግና ኢኮኖሚውን በማነቃቃት ዓይነተኛ ሚና መጫወቱን አንስተዋል።

የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያ እንዲወሰን መደረጉ በተለይም የዝቅተኛ ደመወዝ ተከፋይ ዜጎችን ጫና ውስጥ እንዳይከት መንግስት የተለያዩ እርምጃዎችን መውሰዱንም አስታውሰዋል።

መንግስት የቋሚ ደመወዝ ተከፋይ ዜጎችን የኑሮ ጫና ለማቃለል ቁርጠኛ አቋም ይዞ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከመስከረም ጀምሮ የተደረገው ማሻሻያም የዚህ ማሳያ ነው ብለዋል።

የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሸን ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ የመንግስት ተቋማትን አደረጃጀትና አሰራር በማዘመን በክህሎትና በባህሪ የበቃ የሰው ኃይል አስተዳደርና ልማትን በመዘርጋት ለተገልጋዩ ኅብረተሰብ ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት ለመስጠት የተለያዩ ሪፎርሞች እየተካሄዱ ናቸው።

የማሻሻያ ሪፎርሙ የገንዘብ ሚኒስቴርን ጨምሮ በስምንት ተቋማት በደረጃ ሲተገበር እንደነበርም አስታውሰዋል።

ከተቋማቱ መካከል የገንዘብ ሚኒስቴር የተለያዩ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ጨርሶ ከዛሬ ጀምሮ ወደ ሙሉ ትግበራ መግባቱን አድንቀዋል።

ሚኒስቴሩ በአተገባበር ሂደት የተሻለ አፈፃፀም በማስመዝገብ ለሌሎች አርአያ ሊሆን እንደሚገባ አመልክተዋል።

ከሶስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ለሚበልጡ የመንግስት ሰራተኞች የደመወዝ ማሻሻያ ለማድረግ ተጨማሪ 160 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግና ይህም የመንግስትን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል።

የመንግስት ሰራተኛው ስራውን በውጤታማነት በመፈፀም ለአገራዊ ዕድገት የድርሻውን እንዲወጣ መጠየቃቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ኮሚሽነሩ ሪፎርሙ የመንግስት ተቋማት አሰራራቸውን በማዘመን ለተገልጋዩ ኅብረተሰብ ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሰረታዊ ለውጥ ለማምጣት ያስችላል ብለዋል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review