የቡሳ ጎኖፋ ስርዓትን የበለጠ የሚያጠናክሩና የህብረተሰቡን የባለቤትነት ስሜት የሚያሳድጉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ ኃላፊ አቶ መሀመድ ጁንዳ ተናገሩ።
የቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ የስራ ኃላፊዎች የክልሉ ኮሙኒኬሽን በሚያዘጋጀው ‘ጉሚ በል በሎሚ’ በተሰኘ መድረክ ስርዓቱ ህዝባዊ መሰረት እንዲኖረው እየተሰሩ ባሉ ስራዎች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የክልሉ ቡሳ ጎኖፋ ኃላፊ አቶ መሀመድ ጁንዳ እንዳሉት ከገዳ ስርዓት የመነጨው እና የእርስ በርስ መረዳጃ ስርዓት የሆነው ቡሳ ጎኖፋ ስርዓት እንዲጠናከር እየተደረገ ነው።
በተለይም ህዝቡ ከሌላ አካል እርዳታ እና ድጋፍ ከመጠበቅ ወጥቶ በራሱ መንገድ የሚያጋጥሙትን ችግሮች ተቋቁሞ ማለፍ እንዲችል እየተደረገ ነው ብለዋል።
እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴም ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ 27 ሚሊዮን አባላትን ማፍራቱን ጠቅሰው፤ ከእነርሱ ከሚገኘው መዋጮ እና በስጦታ መልክ በሚበረከትለት ተቋሙ እየተጠናከረ መምጣቱን ተናግረዋል።
በዚህም በክልሉ አጋጥመው የነበሩ ሰው ሰራሽ እና ተፈጥሯዊ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋም መቻሉን ገልጸው፤ በስርዓቱ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን ገልጸዋል።
በ2017 በጀት ዓመት ተቋሙ ከክልሉ አልፎ ለሌሎች ክልሎች ጭምር ድጋፍ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል።
በአጠቃላይ በቡሳ ጎኖፋ ስርዓት ህዝቡ እርስ በርስ እንዲረዳዳ፣ አብሮነትና መተጋገዝ እንዲጎለብት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የተናገሩት ኃላፊው ችግሮችን በራስ አቅም ለማለፍ የሚያስችል አቅም እየተገነባ መሆኑን መግለጻቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡