ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት ዛሬ ወጣቶቻችን የመጪው ዘመን የአየር ንብረት አጀንዳዎችን የሚቀርጹበትን “የአፍሪካ ወጣቶች የአየር ንብረት ጉባኤ 2025”ን በመዲናችን አዲስ አበባ በይፋ ከፍተናል ብለዋል፡፡
አፍሪካ ለበካይ ጋዝ ልቀት ያላት አስተዋጽኦ ዝቅተኛ ቢሆንም፣ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ በድርቅ፣ በበረሃማነት፣ በምግብ ዋስትና ችግር፣ በጎርፍና በሌሎች አደጋዎች እየተፈተነች ትገኛለች።
አህጉራችን አፍሪካ ችግሮች ቢደራረቡባትም የተጨባጭ መፍትሔዎች አህጉር ስለመሆኗ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ልማት ትግበራና ስኬት ሁነኛ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ኢኒሺየቲቭ በተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር 48 ቢሊዮን የሚጠጉ ችግኞችን ተክላለች፤ ለሚሊዮን ወጣቶቿ የሥራ ዕድል ፈጥራበታለች፤ የምግብ ዋስትናንም ማረጋገጥ ጀምራለች።
ሀገራችን ለቀጣናው ታዳሽና የንጹህ ኢነርጂ እያቀረበች መሆኗም አፍሪካ በሕዝቦቿ ንቁ ተሳትፎ ራዕይዋን እንደምታሳካ ተጨባጭ የተግባር ምሳሌ ነው።
ወጣቶች የአፍሪካ የጥንካሬና የተስፋ ምንጭ በመሆናቸው የማትበገር አፍሪካን ለመገንባት ፈጠራ መር መፍትሔዎችን በማፍለቅና በትብብር መሪ ሚናቸውን አጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡