ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ተጠናቆ ለምርቃት መብቃቱን ምክንያት በማድረግ በህብረት ችለናል በሚል መሪ ቃል በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ እየተካሄደ ይገኛል ፡፡
የክልሉ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ መለሰ በየነ ለአዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ ዲጂታል ሚዲያ እንደገለጹት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ህዝብ ግድቡ በርካታ ዉጣ ዉረዶችን አልፎ ለምረቃ በመብቃቱ ደስታዉን በመግለጽ ላይ ይገኛል፡፡
ይህንኑ የተመለከተ የህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ በክልሉ ሁሉም ከተሞች በመካሄድ ላይ መሆኑን በመጥቀስ በአሶሳ ከተማ እየተካሄደ ባለው የድጋፍ ሰልፉ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀገር ሽማግሌዎች ፣ የጸጥታ አካላት ፣የመንግስት ሠራተኞች እና የከተማው ነዋሪዎች መሳተፋቸዉን ገልጸዋል፡፡
በድጋፍ ሰልፉ ላይ ግድቡ የእኔ ነው፣ ህዳሴ ግድባችን በራሳችን የተገነባ የአንድነታችንና የአብሮነታችን ምሰሶ ነው እና ሌሎች መልእክቶች እየተላለፉ እንደሚገኙም አንስተዋል፡፡
የተለያዩ የህብረሰተብ ክፍሎችን ያሳተፈዉ የድጋፍ ሰልፍ በአሶሳ ከተማ፤ በመተከል እና ካማሺ ዞን በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡
በወንድማገኝ አሰፋ