የመስቀል ወፍ ፡- በኢትዮጰያውያን ዘንድ ያላቸው ትርጓሜ እና ትስስር

You are currently viewing የመስቀል ወፍ ፡- በኢትዮጰያውያን ዘንድ ያላቸው ትርጓሜ እና ትስስር

‎AMN – መስከረም 15/2018 ዓ.ም

‎በቆይታ ወይም በረዥም ግዜ ብቅ ለሚሉ ወዳጆች ምነው እንደመስቀል ወፍ አልፎ አልፎ ብቅ ትላለህ ይባላል።

‎ይህ ብቻ አይደለም እንደ መስቀል ወፍ የሚወዱት ሰው ከአይናቸው ሲሰወር እንዲህ እያሉም ይዘፍናሉ።

‎የመስቀል ወፍ እና አንቺ ልጅ ያው ናችሁ በአመት አንዴ በቻ ብቅ ትላላችሁ …………

‎በድምፃዊው ሰማህኝ በለው ከተዜመው ስንኞች ውስጥ የተወሰደ የዘፈን ግጥም ነው ። በዚህ ግጥም በዓመት አንዴ ላያት እንስት የተዜመ ነው።

‎”መስቀል ወፍ እና የአደይ አበባ፣::

‎ቀጠሮ እንዳላቸው መስከረም ሲጠባ” እንዲል ገጣሚው የሁለቱን በወርሀ መስከረም ብቅ ማለታቸውን ይገልፃል ። ‎አንድ ሰው ለረጅም ጊዜ ጠፍቶ ቆይቶ ድንገት ሲከሰት ‘ ምነው የመስቀል ወፍ ሆንክ’ ይባላል።

‎ይህም ለረጅም ጊዜ ሳይታይ ወይም ጠፍቶ ቆይቶ መታየትን ለማመልከት ማህበረሰቡ የሚጠቀምበት አባባል ነው። አእዋፋትን በቅርበት የሚያጠኑት ባለሞያዎችም ከዚህ አባባል ጋር ይስማማሉ ።

‎የመስቀል ወፍን በተመለከት የኤ ኤም ኤን ዲጅታል በኢትዮጰያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር እና የእንስሳት ተመራማሪ ከሆኑት ተስፉ ፈንከሳ (ዶ/ር) ጋር ቆይታ አድርጓል።

‎የመስቀል ወፎች በኢትዮጰያ ብቻ የሚገኙ ናቸው? ነው ወይስ በሌሎች አገሮች ይገኛሉ በሚለው የብዙዎች ጥያቄዎች ላይ ምላሽ ሰጥተዋል ። የመስቀል ወፍ በኢትዮጰያ ብቻ ሳይሆን ከሌላ ቦታ የሚሰደዱ፤ በአፍሪካ በታችኛው የሰሃራ በረሃ አካባቢ በብዛት የሚገኙ መሆናቸውን ተመራማሪው ይጠቁማሉ ።

‎የእነዚህ አዕዋፋት ስያሜያቸው ዊዶ( widow bird)፣ ቢሾኘ (bishop)፣ ኢንዲጎ (Indigo) እና ዋይዳህ (whydah) የሚባሉ የወፍ ዓይነቶች በአንድ ላይ የመስቀል ወፍ በመባል እንደሚታወቁ አስረድተዋል ፡፡

‎የመስቀል ወፍ ከ10 በላይ ዝርያዎች ያሏቸው ሲሆን፤ እነዚህ የወፍ ዝርያዎች በመስከረም ወር መግቢያ ወቅታዊ መራቢያቸው በመሆኑ የፆታ ጓደኞቻቸውን ለመሳብ ሴቶቹ ቀለማቸውን እንደወቅቱ እንደሚቀያይሩም ይገልፃሉ፡፡

‎ለዚህም ነው በሀገራችን መስከረም ወር የተለያዩ ህብረ ቀለማት ያላቸው ወፎች ይከሰታሉ የሚሉት ተመራማሪው፣ ከዚህ በተጨማሪም የተወሰኑ ወፎች እንቁላሎቻቸውን በሌሎች የወፍ ጐጆዎች ሄደው በመጣልም ይራባሉ ብለዋል ፡፡

‎ብዙዎቹ ከጥቁር ውጭ ጠቆር ያለ ቡኒ እግሮች እንዳላቸው፣ ልዩነታቸውም መንቆራቸው እና እግሮቻቸው ላይ ነው በሚታየው ሲሉም ተናግረዋል ። የመስቀል ወፍ ዝርያዎች ግን በመጠን፣ በመንቆር፣ በላባቸው ቀለም እና በእግራቸው ቀለሞች ይለያያሉ። የመራባት ሁኔታ ላይ ግን በአንድ አካባቢ የሚኖሩ በተሻለ የመቀራረብ ዕድል እንዳላቸው ይገመታል።

‎የመስቀል ወፍ ተባዕቶቹ የወፎ ዝርያዎች የላባ ቀለም በመቀያየር እንስቶቹን የበለጠ በመሳብ የመራቢያ ወቅታቸው መምጣቱንና የሚያበስሩበት ወቅት መስከረም ወር አካባቢ መሆኑ ይገለፃል ፡፡

‎በአገራችንም ታዲያ በመስከረም ወር የወፍ ዝርያዎች የሚራቡበት ወርቃማ ጊዜ በመሆኑ የወፎቹ ዝማሬ ከአንፀባራቂ ቀለም ጋር ተያይዞ ወሩን የተለየ ትዝታ የሚፈጥሩበት ይሆናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

‎በሔለን ተስፋዬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review