ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በሁለቱ ምክር ቤቶች የጋራ የመክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር በሀገሪቱ አንዳንድ አከባቢዎች የሚታዩ ግጭቶችን በመፍታት ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ መንግሥት በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል።
የተጀመረው የሃገራችን ማንሰራራት ጉዞ በፅኑ መሰረት ላይ እንዲገነባ መንግስት ነጻ እና ገለልተኛ ተቋማት ማቋቋም ላይ በቁርጠኝነት ይተጋል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ ብሔራዊ የፀጥታ እና የደህንነት ተቋማት የስርዓት ለውጥን የሚሻገሩ እና የሃገርን ቀጣይነት የሚያረጋግጡ ብርቱ ተቋማት እንዲሆኑ በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡
በአንዳንድ ቦታዎች የሚታዪ ግጭቶችን የሰላም መንገዶችን በመከተል ለመፍታት እየተሰራ እንደሚገኝ የገለፁት ፕሬዝዳንቱ፤ የዛሬውን ግጭት በማሸነፍ ለነገው ትውልድ ቂም እና ቁርሾ ላለማውረስ፤ በብልሃት እና በትዕግስት ለዘላቂ ሰላም እንደሚሰራም ጠቁመዋል፡፡
አሁን ላይ የሚከሰቱና እስከዛሬ የነበሩ ችግሮችን ይፈታል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የሀገራዊ ምክክር ስኬታማ እንዲሆን መላው ሕዝብ የበኩሉን እንዲወጣም ፕሬዚዳንቱ ጥሪ አቅርበዋል።
መንግስት የዜጎችን ዋስትና ከማስጠበቅ አንጻር የፍርድ ቤት አገልግሎትን ዲጂታል የማድረጉ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በሁለቱ ምክር ቤቶች የመክፈቻ ስነ-ስርአት ላይ ገልፀዋል ፡፡
በ- ፍሬህይወት ብርሃኑ