እንደ ስሟ ዉብ የሆነችዉን አዲስ አበባ አሁን ገና አየን

You are currently viewing እንደ ስሟ ዉብ የሆነችዉን አዲስ አበባ አሁን ገና አየን

‎AMN- መስከረም 27/2018 ዓ.ም

‎የአዲስ አበባ ውበት ከሚያጎሉ ትዕይንቶች መካከል የአደባባይ በዓላት ግንባር ቀደም ናቸው ።

‎በአዲስ አበባ በወርሃ መስከረም ከመሰቀል በዓል ቀጥሎ የመዲናዋን ውበት ካጎሉ በዓላት አንዱ በድምቀት የተከበረው የኢሬቻ ሆረ ፊንፊኔ በዓል ነው።

‎በዚሁ በዓል ላይ የአዲስ አበባ ውበት ስለመጎምራቱ በርካቶች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

‎ከአሪ ብሔረሰብ ብርቅዬ አቀንቃኞች መካከል አንዱ የሆነው ታሪኩ ጋንኪስ፣ ወይም ዲሽታ ግና የአዲስ አበባ ውበት ከግዜ ወደ ጊዜ በመጉላቱ መደነቁን ተናግሯል።

‎የአዲስ አበባ በኮሪደር ልማት መዋብ ለኢትዮጰያውያን መሆኑን አንስቷል።

‎ልማት እና ሰላም ለህዝብ የሚጠቅም ነገር በመሆኑ ይህንን ተግባር ማስቀጠል እንደሚገባም ነው የተናገረው።

‎መዲናዋ በጥሩ ሁኔታ አምራ እና ተውባ ተመልክቻታለሁ ያለው ድምፃዊው፣ አዲስ ልብስ ለብሰን እንደሚያምርብን ሁሉ ከተማዋም ስትለማ እንዳማረባት ገልጿል

‎ልማቱ ለሌሎች ሀገራችን ይችህ ናት እንድንል እንድንኮራባት እንድንመካባት ያደርጋል ሲል ተናግሯል።

‎ኢሬቻን በሆረ ፊንፊኔ ለማክበር ከሲዳማ ክልል የመጡት አቶ አሰፋ ኪያ በበኩላቸዉ በአዲስ አበባ የተሰሩ መሰረተ ልማቶች ከዚህ በፊት ከነበረው ፍፁም ልዩነት እንዳለው ጠቅሰዋል።

‎በአጠቃላይ በኮሪደር ልማት የተሰሩ ስራዎች የአፍሪካ መዲና የዓለም የዲፕሎማቶች መቀመጫነቷን በተግባር ያረጋገጠ ነው ብለዋል።

‎አዲስ አበባ እንደስሟ አብባ አይቻለሁ ያሉት የበዓሉ ተሳታፊ፣ ልማቱ ለበዓሉ ልዩ ድባብ እንደፈጠረም ጠቅሰዋል።

‎በተለይም በዓሉ የሚከበርበት መልካ ሆረ ፊንፊኔ በዚህ መልኩ መሰራቱም በዓሉን ልዩ ውበት አጎናፅፎታል በማለት አስረድተዋል።

‎አርቲስት አበበች አጀማ፣ በሆረ ፊንፊኔ ኢሬቻ በዓል ለማክበር ከተገኙ ታዋቂ የአፋን ኦሮሞ የኪነ-ጥበብ ሰዎች መካከል አንዷ ናት።

‎በዓሉ ከተሰራው የመሰረተ ልማት ጋር ተዳምሮ ለከተማዋ ልዩ ውበት ያላበሰ ሲሆን፣ በዓሉን በአንድነት፣ በፍቅር እና በደስታ ማክበራቸውን ተናግራለች

‎የአዲስ አበባ ከተማ የኮሪደር ልማትን ስትመለከት ውጭ ሀገር እንደሚመስላት ገልፃ፣ ከተማዋ እንደ ስሟ አዲስ መሆኗ እንዳስደሰታት ተናግራለች

‎አዲስ አበባ ሌላ አዲስ ከተማ መስሏል መልካ ሆረ ፊንፊኔ ደግሞ ተጨማሪ ድምቀት ፈጥሯል ያሉት የኦሮሞ አባገዳዎች ሰብሳቢ አባ ገዳ ወርቅነህ ተሬቻ ናቸው።

የመጫ አባገዳ ወርቅነህ እንደተናገሩት ፣ በዓሉ የሚከበርበት ስፍራ መግቢያው እና መውጫው በአግባቡ የተስተካከለ እና ያማረ መሆኑን ጠቅሰዋል።

‎ከእንጦጦ ጀምሮ የወንዙ ዙሪያ ሁሉ አረንጓዴ መልበሱ ለከተማዋ ተጨማሪ ውበትን አላብሷታል ብለዋል።

‎በሔለን ተስፋዬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review