በአማራ ክልል የተደራጁ ወንጀሎችንና የፀረ-ሰላም ኃይሎችን እንቅስቃሴ ለመከላከል የሚያስችል አቅም ማደጉን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽነር ዘላለም መንግስቴ (ዶ/ር) ገለጹ።
የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር ዘላለም መንግሥቴ (ዶ/ር) እንደገለጹት የክልሉ ፖሊስ የሕግ ማስከበር አቅሙን ለማጠናከር እና ለህዝብ የሚሰጠውን አገልግሎት ለማሻሻል ሁለንተናዊ ሪፎርም አድጓል።
ሪፎርሙ የፖሊስን ተቋማዊ አቅም በማጠናከር ለህዝብ የሚሰጠውን አገልግሎት ጥራት ለማሻሻል ያለመ መሆኑን ተናግረው፤ ይህም ፖሊስ እንደ ህዝባዊ ተቋም ውጤታማ የሕግ ማስከበር ስራ እንዲያከናውን ያስችለዋል ነው ያሉት።
የፖሊስ ሥራዎችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ የአገልግሎት አሰጣጡን ፈጣንና ግልጽ ለማድረግ የዲጂታል ለውጥ ሥራዎች ማድረጉንም ኮሚሽነሩ ጠቅሰዋል። የፖሊስ መዋቅርን በማዘመን የሰው ኃይል ምደባን በተዘጋጀ መመሪያና ስታንዳርድ መሠረት መዋቀሩን ነው ያስረዱት።
ገለልተኛ የፖሊስ አገልግሎት እና የሕዝብን አመኔታ እና ፍትሕን የማስፈን አቅምን ማጠናከር ላይ ትኩረት ተደርጓል ሲሉም አብራርተዋል። ተቋማዊ ሪፎርሙ በክልሉ የተደራጁ ወንጀሎችንና የፀረ-ሰላም ኃይሎችን እንቅስቃሴ ለመከላከል የሚያስችል አቅም እያሳደገ እንደሆነ አስታውቀዋል።
በዚህም በክልሉ ሰላም እየሰፈነ መምጣቱን ተናግረው፤ አሁን ላይ የልማት ተግባራትን ጨምሮ የመማር ማስተማር ስራዎችን በተረጋጋ ሁኔታ ለማከናወን መቻሉን ተናግረዋል። ለአርሶ አደሩ የግብርና ግብዓቶች በአግባቡ ተደራሽ በመሆናቸው የእርሻ ሥራው በጥሩ ሁኔታ መከናወን መቻሉን ገልፀዋል።
በክልሉ አስተማማኝ ሰላም ለማረጋገጥ የክልሉ የፀጥታ ምክር ቤት ስልታዊ አቅጣጫ ማስቀመጡንም ተናግረዋል። በዚህም የክልሉ የፀጥታ መዋቅር ከሀገር መከላከያ ሰራዊት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ኮሚሽነሩ ማስታወቃቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡ በክልሉ የውጭ ጠላት ተልዕኮን አንግበው የሚንቀሳቀሱ ባንዳዎችን የማፅዳት ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ኮሚሽነሩ ተናግረዋል።