ኢትዮጵያውያን ጀግንነታቸውን ሀገር በማልማትና በመቀየር ሊያሳዩ ይገባል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከፌዴራል እና ክልል አመራሮች ጋር የገጠር ኮሪደር ስራዎች ላይ ውይይት አድርገዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዚህ ዘመን የኢትዮጵያውያን ጀግንነት ሀገርን በማልማትና በመቀየር እንዲሁም ህዝብን መቀየር ሊሆን እንደሚገባ ገልጸዋል።
ለም ሀገር እና መሬት ይዘን ልንለምን አይገባም፤ የልመና ታሪካችንና የዜጎችን ህይወት መለወጥ የምንችለው ተግቶ በመስራት ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያውያን ለበጎ አላማ በመደመር በሀገር ደረጃ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት መስራት እንዳለባቸውም ነው ያመላከቱት።
ቀጣዩ ትውልድ የተሻለ ነገር እንዲረከብ ዛሬ ላይ ጠንክሮ መስራት እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል።
ለማህበረሰብ የሚታይ እና የሚጨበጥ ስራ ለመስራት የአመራር ቁርጠኝነት ወሳኝ እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል።
ውድድር በልማት እና በስራ ሊሆን ይገባል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ክልሎች ባለቸው አቅም በመስራት የዜጎችን ህይወት ከቀየሩ ያለ ምንም ጥርጥር የበለጸገች ኢትዮጵያን ማየት እንደሚቻል ተናግረዋል።
ኢትዮጵያውያውን አንችልም የሚለውን ሀሳብ እና አመለካከት መስበር ይገባናል፤ ኢትዮጵያውያን መቻላችንን ድሮም አሳይተናል አሁንም ችለን ማሳየት አለብን ብለዋል።