ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእከት ዛሬ ለኪነጥበብ ቤተሰቦች እና ለከያኒያን ተጨማሪ ብስራት የሆነውን አዲሰ እና እጅግ ዘመናዊ አዲስ ሲኒማ ኮምፕሌክስ ህንፃ ግንባታ አጠናቅቀን መርቀን ለአገልግሎት ክፍት አድርገናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በአይነቱ የመጀመሪያ እና እጅግ ዘመናዊ የሆነውን የህፃናትና ወጣቶች ቴአትርና ሲኒማ ኮምፕሌክስ መርቀን ብዙም ሳንቆይ፣ ዓለም በፊልም ኢንዱስትሪው የደረሰበት ደረጃ ለመድረስ በያዝነው ዕቅድ መሰረት፣ ለኪነጥበብና ለከያኒያን ትልቅ የምስራች የሆነውን አዲስ እና እጅግ ዘመናዊ ሲኒማ ኮምፕሌክስ ህንፃ በዛሬው ዕለት ስራ አስጀምረናል ብለዋል፡፡
አዲስ ሲኒማ ኮምፕሌክስ ህንፃ፣ ባለ 15 ወለል ሲሆን የህንፃው አጠቃላይ ስፋት 24,000 ካ.ሜ ሆኖ ባለ አራት ወለል የመኪና ማቆሚያ የያዘ ነው። 592 ህፃናትንና 887 አዋቂዎችን የመያዝ አቅም ያላቸው ሁለት የሲኒማ አዳራሾችን ጨምሮ በቂ የሆነ የድምፅ ማስተላለፊያ ሲስተም፣ ዘመናዊ የመብራት ስርጭት፣ የአየር መቆጣጠሪያ መሳሪያዎችን አካቷል።
በተጨማሪም፤ ለቢሮዎች፣ ለእስቱዲዮ፣ ለሥዕል እና አርት ጋለሪ፣ ለቤተመፃሕፍት እና ለተለያዩ ተያያዠ አገልግሎቶች፣ ለካፍቴሪያ፣ ለሱፐርማኬት፣ ለምግብ ቤት፣ ለሱቆች፣ ለውበት ሳሎን፣ ለባንክ አገልግሎት፣ የትኬት መሸጫ ቢሮዎች እና ለጉብኝት አገልግሎት የሚውሉ ክፍሎችንም አሟልቷል ብለዋል፡፡
በቅጥር ጊቢውም የልጆች መጫወቻ የስፖርት ሜዳ፣ የመኪና ማቆሚያና አረንጓዴ ስፍራዎችን ጨምሮ ለማስታወቂያ የሚሆኑ ስክሪኖች እና ዘመናዊ ሊፍቶች እንዲሁም የፓርኪንግ ቴክኖሎጂዎች ተገጥመውለታል።
በዚህ አዲስና ዘመናዊ ለትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ስራ ላይ የተሳተፋችሁ አማካሪዎች፣ ተቋራጮች እና የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ አመራሮች እና ሰራተኞች፣ ደከመን ሰለቸን ሳትሉ የተሳተፋችሁትን በሙሉ በከተማ አስተዳደሩ እና በራሴ ስም ላመሰግናችሁ እውዳለሁ ብለዋል፡፡