የኬኒያ ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ የራይላ ኦዲንጋን ህልፈት አስመልክቶ ለ7 ቀናት የሚቆይ ብሔራዊ ሀዘን አውጀዋል።
አንጋፋው የኬኒያ ፖለቲከኛ ራይላ ኦዲንጋ የህክምና ክትትል ለማድረግ በሄዱበት ህንድ ህይወታቸው ማለፉ ይታወሳል።
በፈረንጆቹ 2010 በጭንቅላታቸው ላይ የቀዶ ጥገና ህክምና ካደረጉ ጀምሮ በተደጋጋሚ ለህክምና ክትትል ወደ ህንድ ሲያቀኑ የቆዩት ኦዲንጋ በልብ ድካም ህይወታቸው ማለፉ ተሰምቷል።
ፕሬዝዳንት ሩቶ፤ ራይላ ኦዲንጋ ለሀገራቸው ላበረከቱት ከፍተኛ አበርክቶ ብሔራዊ ሀዘን በታወጀባቸው ቀናት ውስጥ የኬኒያ ሰንድቅ አላማ ዝቅ ብሎ እንደሚውለበለብ ተናግረዋል።
በተጨማሪም በመጪዎቹ ቀናት ፕሬዝዳንቱ የነበራቸውን ህዝባዊ ስብሰባዎች እንዲራዘሙ ማድረጋቸውንም ገልጸዋል።
በኬኒያ ፖለቲካ ውስጥ ብርቱ ተፎካካሪ የነበሩት ራይላ ኦዲንጋ ከ2008-2013 ሀገሪቷን በጠቅላይ ሚኒስትርነት አገልግለዋል።
በዳዊት በሪሁን