በማኅበራዊ የመገናኛ መተግበሪያዎች አማካኝነት የማጭበርበር ወንጀሎች ፈጽመዋል የተባሉ አካላት በሕግ እንዲጠየቁ እየሠራ መሆኑን የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ።
አንዳንድ በማጭበርበር ድርጊት ላይ የተሰማሩ ሰዎች ከግለሰቦች ዕውቅና እና ፈቃድ ውጭ በሞባይሎቻቸው ውስጥ በመግባት የግለሰቦቹን የማኅበራዊ መገናኛ መተግበሪያዎች (እንደ ዋትስአፕ እና ቴሌግራም የመሳሰሉትን) ምስጢራዊ መረጃዎች በመስረቅ የገንዘብ ማጭበርበር ድርጊት ላይ መሰማራታቸውን አገልግሎቱ ገልጿል።
ግለሰቦቹ የማኅበራዊ መገናኛ መተግበሪያዎችን ከተቆጣጠሩ በኋላ እውነተኛ የአካውንት ባለቤት በመምሰል በግለሰቦቹ ስልኮች ተመዝግበው ለሚገኙ ቤተሰቦች፣ ዘመዶች፣ ጓደኞች፣ እና የሥራ ባልደረቦች ገንዘብ እንደተቸገሩ የሚገልፅ የጽሑፍ መልዕክት በመላክ ለዚሁ የማጭበርበር ዓላማ ወደ ተዘጋጀ የባንክ አካውንት እንዲላክላቸው ያደርጋሉ ብሏል፡፡
የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት የደረሱትን ጥቆማዎችን መሰረት በማድረግ በወንጀል ድርጊቱ ላይ የተሳተፉ አካላትን በመለየት እና በመከታተል በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ከሚመለከታቸው ባለ ድርሻ ተቋማት ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑን ለኤኤምኤን በላከው መረጃ አስታውቋል።
ሕብረተሰቡም ይህን የማጭበርበር ድርጊት ለመከላከል ወደ ስልኩ ለሚደርሱ መልዕክቶች ምላሽ ከመስጠቱ አስቀድሞ በተለያዩ መንገዶች የመልዕክቱን ትክክለኛነት በማረጋገጥ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ አሳስቧል።
እንዲሁም ከሚመለከታቸው ተቋማት የሚተላለፉ የጥንቃቄ መልዕክቶችን በመከታተል ራሱን ከወንጀል ድርጊቶች እንዲጠብቅ እና ወንጀል ተፈፅሞ ሲገኝም ለሕግ አስከባሪ አካላት እንዲያሳውቅ ጥሪ አቅርቧል።