አለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ በ2025 ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት ከሚያስመዘግቡ ከሰሃራ በታች ከሚገኙ ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ እንደምትሆን በትንበያው አስቀምጧል።
ተቋሙ በአለም አቀፍ እና በውስጣዊ ጉዳዮች የቀጠናው ኢኮኖሚ ፈተና እያስተናገደ ቢሆንም የተረጋጋ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገቡን ይቀጥላል ብሏል።
በማክሮ ኢኮኖሚ እየታየ የሚገኘው መረጋጋት አካባቢው በ2025 የ4.1 በመቶ እድገት እንዲያስመዘግብ የሚያስችለው ነው ያለው ሪፖርቱ፤ ይህ እድገት በቀጣዩ አመት ጭማሪ እንደሚያስመዘግብ በትንበያው አመላክቷል።
የተሻሻለ የሀገር ውስጥ ገቢ አሰባሰብ ፣ ጠንካራ የብድር አስተዳደር እና ሌሎች የገንዘብ ፖሊሲዎች አተገባበር ኢትዮጵያን ጨምሮ በሌሎች የቀጠናው ሀገራት መሻሻል እያሳየ እንደሚገኝ ጠቁሟል።
በዚህ መሰረት በተያዘው የፈረንጆቹ አመት (2025) ኢትዮጵያ 7.2 በመቶ እድገት በማስመዝገብ በቀጠናው ከሚገኙ ሀገራት ቀዳሚ ስትሆን ሩዋንዳ በ7.1 በመቶ ትከተላለች።
ቤኒን ፣ ኡጋንዳ ፣ ኮትዲቯር ዚምቧቡዌ ፣ ሴኔጋል ፣ ዛምቢያ፣ ዲሞክራሲያዊት ኮንጎ እና ኬኒያ አወንታዊ እድገት ያስመዘግባሉ የተባሉ ሀገራት ናቸው።
በዳዊት በሪሁን