ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልዕክት የባሌ ዞን የመጀመሪያ ቀን ጉብኝት ያሳየን በድንቅ ተፈጥሮ እና በልማት ሥራ እድገት መካከል ያለውን መስተጋብር ነው ሲሉ ገልጸዋል።

በአስደናቂ ብዝኅ መልኩ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ የቱሪዝማችን አንዱ የማዕዘን ድንጋይ ሆኖ ቀጥሏል።
ይህ እምቅ አቅም በፓርኩ እምብርት ላይ የተገነባው የዲንሾ ሎጅ በቅርቡ ሲጠናቀቅ የበለጠ ይጠናከራል።
በአቅራቢያው በመገንባት ላይ ያለውና በቅርቡ የሚጠናቀቀው የሶፍኡመር ሎጅ ቱሪዝምን የኢኮኖሚያችን ቁልፍ መሪ አድርጎ ያስቀመጠው የኢትዮጵያን የ10 አመት ስትራቴጂክ እቅድ የሚተገብር ነው።

ሎጁ በሶፍኡመር ዋሻ የጎብኝዎችን ቆይታ ከፍ የሚያደርጉ እና የመዝናኛ አገልግሎት መስጫዎች በሶፍኡመር ዋሻ ልማት ፕሮጀክት እገዛ የሚዘጋጁበት ነው።
በመንገድ መሠረተ ልማት ረገድ የሮቤ -ጎሮ- ሶፍኡመር – ጊኒር መንገድ የማሻሻያ ፕሮጀክት ከፍተኛ አምራች የሆኑትን የምሥራቅ ባሌ እና የባሌ ዞኖችን ምርታቸውን ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ የሚያገናኝ ነው።

ይህ መሥመር ተደራሽነትን እና የኢኮኖሚ ተያያዥነትን ብቻ ሳይሆን እንደሶፍኡመር ዋሻ እና የባሌ ተራሮች ወደ መሰሉት ዐበይት የመስኅብ ሥፍራዎች ጉዞን የሚያሳልጡ ናቸው ሲሉ ገልጸዋል።
ድርብ አስፋልት ንጣፍ ባለው ከፍ ያለ ደረጃ የተገነባው መንገድ 29 ኪሎሜትር የከተማ እና የገጠር መንገድን የሚያካትት ብሎም ከ12 እስከ 140 ሜትር ርዝመት ያላቸው አምስት ድልድዮች የተሠሩበት ነው።

የቀኑን ጉብኝታችንን የወይብ ወንዝ የጎርፍ መቆጣጠሪያ ፕሮጀክትን በመመልከት አጠናቀናል ብለዋል።

ፕሮጀክቱ በሶፍኡመር ዋሻ የሚጓዘውን የወንዙን የውሃ ፍሰት በመቆጣጠር አመቱን ሙሉ ወደ ዋሻው የሚደረግ ጉዞ እንዳይስተጓጎል ለማድረግ ብሎም የዋሻውን ሥነምኅዳር ለመጠበቅ ታልሞ የተሠራ ነው። ሁሉም ሥራዎች ቀጣይነት ላለው ልማት ያለንን ጽኑ አቋም እና ተግባር የሚገልጡ ናቸው ሲሉ ገልጸዋል።