ሰብዓዊነትን አስቀድመው አርአያነት ያለው ተግባር የፈጸሙ ደንብ አስከባሪዎች እውቅና ተሰጣቸው

You are currently viewing ሰብዓዊነትን አስቀድመው አርአያነት ያለው ተግባር የፈጸሙ ደንብ አስከባሪዎች እውቅና ተሰጣቸው

‎AMN- ጥቅምት 8/2018 ዓ.ም

በበጎ ተግባር ላይ ተሰማርተው አርአያነት ያለው ተግባር የከወኑ የደንብ አስከባሪ ኦፊሰሮች ተግባራቸው ለሌሎች አስተማሪ በመሆኑ እውቅና እና ሽልማት እንደተበረከተላቸው ‎የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ ሻለቃ ዘሪሁን ተፈራ ገልጸዋል፡፡

የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ጉልህ የሰብአዊነት ተግባር ለፈጸሙ የደንብ ማስከበር ኦፊሰሮች እውቅና እና ሽልማት አበርክቷል፡፡

‎የባለስልጣኑ ዋና ስራ አስኪያጅ ሻለቃ ዘሪሁን ተፈራ፣ በበጎ ተግባር ላይ ተሰማርተው አርአያነት ያሳዩ የደንብ አስከባሪ ኦፊሰሮች ተግባራቸው ለሌሎች አስተማሪ በመሆኑ ሽልማት እንደተበረከተላቸው ገልጸዋል፡፡

‎የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አለማየሁ ሚጀና በበኩላቸው፣ የአዲስ አበባ ደንብ አስከባሪዎች የተሰማሩበትን አላማ የሚያሳኩ፣ ዜጎችን በእኩል ዓይን በማየት እና ሰብአዊነትን በማስቀደም የሚሰሩ ናቸው ብለዋል።

‎በአቃቂ ቃልቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 የሚገኙ፤ ጉድጓድ ውስጥ የወደቀን መንገደኛ በማንሳት መልካም ተግባር የፈፀሙ ሁለት ደንብ አስከባሪ ኦፊሰሮች ያከናወኑት የሰብአዊነት ተግባር ሰሞኑን በማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን መሰራጨቱን ተከትሎ የእውቅና እና ሽልማት የመስጠት ስነ-ስርዓት ተከናውኗል፡፡

‎ከዚሁ ጋር በተያያዘ ደንብን ከማስከበር ተግቧሯ ጎን ለጎን የደንብ ማስከበር ዩኒፎርም በመልበስ በማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን የደንብ ማስከበር ተግባራትን የማስተዋወቅ ስራዎችን የምትሰራ የደንብ ማስከበር ኦፊሰርም ሽልማት ተበርክቶላታል፡፡

‎ከተሸላሚ የደንብ ማስከበር ኦፊሰሮች መካከል ሌንሳ ከቤ፣ ተስፋሁን ሳሙኤል እና ይርጋለም አበባው የፈጸሙት የሰብዓዊነት ተግባር ስላሸለማቸው መደሰታቸውን ገልጸው፣ ሌሎችንም ለበለጠ ሰብዓዊነት እንደሚያነሳሳ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

‎ደንብ አስከባሪዎች ከተሰማሩበት ዋና ተግባራቸው ባሻገር ሰብዓዊነትን አስቀድመው አርአያነት ያለው ተግባር መስራታቸው ሊበረታታ እንደሚገባው በመርሐ-ግብሩ ተመላክቷል፡፡

‎ባለስልጣኑ በአስራ አንዱም ክፍለ ከተሞች በተሰማሩት የደንብ አስከባሪ ኦፊሰሮች አማካኝነት ደንብ መተላለፍን መከላከልና ሰላምና ፀጥታን የማስከበር ተግባራትን እየተወጣ ይገኛል፡፡

‎በፈቃዱ ምስጋናው

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review