የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ከአዲሱ የአፍሪካ ልማት ባንክ ግሩፕ ፕሬዝዳንት ጋር ስትራቴጂካዊ አጋርነት ማጠናከር በሚቻልባቸዉ ጉዳዮች ተወያዩ

You are currently viewing የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ከአዲሱ የአፍሪካ ልማት ባንክ ግሩፕ ፕሬዝዳንት ጋር ስትራቴጂካዊ አጋርነት ማጠናከር በሚቻልባቸዉ ጉዳዮች ተወያዩ

AMN ጥቅምት 9/2018

የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ከዓለም ባንክ እና አይ ኤም ኤፍ አመታዊ ስብሰባዎች ጎን ለጎን የአፍሪካ ልማት ባንክ ግሩፕ ፕሬዝዳንት ሆነው ከተመረጡት ዶክተር ሲዲ ኦልድ ታህ ጋር በስትራቴጂያዊ አጋርነትና የሁለትዮሽ ትብብርን ማጠናከር በሚቻልባቸዉ ጉዳዮች ዙሪያ ውጤታማ ውይይት አድርገዋል።

የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ በኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ እና የኢንቨስትመንት አካባቢን ምቹ ለማድረግ ፣ ቁልፍ በሆኑ ዘርፎች ምርታማነትን ለማሳደግ እና የመንግስትን የአገልግሎት አሰጣጥ አቅም ለማጠናከር እየተሰሩ ባሉ የሪፎርም ስራዎች ላይ ለፕሬዝዳንቱ ገለፃ አድርገዋል።

በአዲሱና በግዙፉ የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ፕሮጀክት ላይ አዳዲስ መረጃዎችን ያካተተ ውይይት ያካሄዱ ሲሆን የተያዘዉን ፕሮጀክት እዉን ለማድረግ የአፍሪካ ልማት ባንክ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ መሆኑን አስረድተዋል።

ሲዲ ኦልድ ታህ የአፍሪካ ልማት ባንክ ግሩፕ ፕሬዝዳንት ሆነው በመመረጣቸው የእንኳን ደስ ያለዎት መልዕክት በማስተላለፍ በአመራር ሰጭነታቸው ሙሉ እምነት እንዳላቸው ገልፀው፣ ፕሬዚዳንቱ ኢትዮጵያን እንዲጎበኙ ጥሪ አቅርበዋል።

ፕሬዝዳንት ዶክተር ሲዲ ኦልድ ታህ በበኩላቸው የኢትዮጵያን የማክሮ ኢኮኖሚ እና ሌሎች ትላልቅ የሪፎርም አጀንዳዎችን አፈፃፀም አድንቀው፣ ባንኩ የሀገሪቱን ትልቅ የለውጥ አጀንዳ በበጀት ድጋፍ፣ በግብርና እና በመሰረተ ልማት ላይ ኢንቨስት በማድረግ በተለይም የአየር ትራንስፖርት ትስስርን በማጠናከር የቀጠናዊ ትስስርና ውህደት እንቅስቃሴዎች ላይ ድጋፍ ለማድረግ ያለውን ዝግጁነት አረጋግጠዋል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review