ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ በምስራቅ ሸዋ ዞን የነበረን ጉብኝት በክረምት የስንዴ ምርት ሥራዎች የተገኘውን ውጤት የምርት አሰባሰቡን በመመልከት ለመገምገም እና የበጋ ስንዴ ሥራ ማስጀመር ላይ ያተኮረ ነበር ብለዋል።
በዚያው አካባቢ የሙዝ፣ ፓፓያ እና አሳ ክለስተር ሥራዎችንም ተመልክተናል።

ነባሩ ባሕላዊ የግብርና ዘዴ አሁንም ያለ ቢሆንም በሰፊው ለማረስ የሚያስችለው ሜካናይዜሽን እያደገ በመሄዱ የአካባቢውን የግብርና ብቁነት እና ምርታማነት እያሳደገ ይገኛል።
ወደኋላ መለስ ብለን የነበረውን አሰራር ስንገመግም እነዚህን መሰል ዘመናዊ ዘዴዎችን ከብዙ አመታት በፊት እንደ ሀገር ጀምረን ቢሆን ኖሮ የግብርና ምርታችን በከፍተኛ ደረጃ የተለየ ይሆን እንደነበር እንረዳለን ብለዋል።
ዛሬ ከአመት ወደ አመት እየጨመረ የሚሄድ ምርታማነት እየተመለከትን እንገኛለን። ለማደግ ምንም አይነት የውጭ ድጋፍ አይመጣም። እውነተኛውን የሀገራችን ለውጥ የሚመራው የራሳችን ጽናት፣ ፈጠራ እና የሥራ ትጋት ነው ብለዋል።