ጽንስ በማህፀን ውስጥ እያለ የደም ልገሳ በማድረግ ስኬታማ የህክምና አገልግሎት ማድረጉን የአበበች ጎበና የእናቶች እና ህፃናት ሆስፒታል ይፋ አደረገ፡፡
እንዲህ አይነት ህክምና ከብራዚል አንድ ጊዜ ከመደረጉ ውጪ በአፍሪካም ይሁን በሌላው ዓለም ያልተሞከረ ህክምና መሆኑን ሆስፒታሉ አስታውቋል።
ጽንሱ አስር ጊዜ ደም የተለገሰለት መሆኑ የህክምናውን ሂደት አስገራሚ ማድረጉም ተሰምቷል።

በሆስፒታሉ ከሌሎች ሃኪሞች ጋር በመሆን ህክምናውን ያደረጉት እና ሂደቱን የመሩት ዶክተር ቴዎድሮስ ጌታሁን ከኤ ኤም ኤን ዜና አዲስ ጋር ባደረጉት ቆይታ ህክምናው በማህጸን ውስጥ ያለ ህጻን ከፍተኛ የደም ማነስ ችግር ሲገጥማቸው በላቦራቶሪ ንጹህ መሆኑ የተረጋገጠ ደም የመተካት ስራ መሆኑን ጠቁመዋል።
ህክምናው ሲጀመር ፅንሱ ገና የ21 ሳምንት እድሜ ብቻ የነበረው መሆኑ እና ሆስፒታሉ የህፃኑ የደም ስሮች በጣም አነስተኛና ደቃቃ በመሆናቸው በቀላሉ አለመገኘታቸው የህክምናውን ሂደት አስቸጋሪ እንዳደረገው ዶክተር ቴዎድሮስ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት እናት እንዲሁም ደም አንሶት የደም ልገሳ የተደረገለት ህጻናን ተወልዶ በጥሩ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ ሆስፒታሉ አስታውቋል።
መሃመድኑር አሊ
 
								 
															 
 
							