ኮሚሽኑ የሃገር ውስጥ የጉብኝት ባህልን ለማስፋት የጉብኝት ንቅናቄ ማስጀመርያ መርሃ ግብር አካሄዷል፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተወጣጡ የሃገርህን እወቅ ክበብ ተማሪዎች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
ትውልዱ በሃገር ውስጥ የሚገኙ የቱሪዝም ስፍራዎችን እንዲጎበኝ እና ታሪኩን እንዲያወቅ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ቢኒያም ታዬ ለኤ ኤም ኤን ተናግረዋል፡፡
አዲስ አበባ በነበራት ውስን የቱሪስት መዳረሻ ቦታዎች ለበርካታ አመታት ለቱሪሰት ማቆያ ሳትሆን መተላለፊ ሆና ቆይታ እንደነበር ያስታወሱት ምክትል ኮሚሽነሩ መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ልዩ ትኩረት መዲናዋ የበርካታ ቱሪዝም መዳረሻዎችን አልምታለች ብለዋል፡፡
እነዚህን የቱሪዝም መዳረሻዎች እንዲጎበኙና የሀገር ውስጥ የጉብኝት ባህልን ለማስፋት ንቅናቄው ተጠናከሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል::
በጉብኝት ንቅናቄ ማስጀመርያ ላይ ብሄራዊ ሙዚየሙን የጎበኙት ተማሪዎቹ ስለሃገራቸው የቱሪዝም ሀብት ያላቸውን እውቀት ያሳደጉበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ኮሚሽኑ በቀጣይ የሀገር ውስጥ የጉብኝት ባህልን ለማጠናከር በተለያዩ ትምህርት ቤቶች የንቅናቄ ተግባሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡
በመሀመድኑር ዓሊ