የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽ/ቤት ከሰራተኞች ስነምግባር እና አገልግሎት አሰጣጥ ጋር የሚነሱ የግብር ከፋይ ቅሬታዎችን መፍታት የሚያስችል የአሰራር ሥርዓት መዘርጋቱን አስታዉቋል፡፡
ጽ/ቤቱ ከአዲስ አበባ የግብር አሰባሰብና የገቢዎች አገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ለሚኖር ማንኛዉም አይነት ቅሬታ መፍታት የሚያስችል አዲስ አሰራር በከንቲባ ፅ/ቤት ስር መዋቀሩን አስታዉቋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የገቢዎች ቢሮ ስር የተዘረጋዉ የቅሬታ አፈታት ስርዓት እንደተጠበቀ ሆኖ በዛ ያልረካ ግብር ከፋይ ከንቲባ ፅ/ቤት ማንኛዉንም አይነት ከገቢ አሰባሰብ ፣ ከሰራተኞች ስነምግባር እና አገልግሎት አሰጣጥ ጋር የሚነሱ የግብር ከፋዮች ቅሬታዎችን ለመፍታት ዘወትር ሐሙስ ኃላፊዎች በተገኙበት የሚደመጥ እና ተጣርቶ ምላሽ የሚሰጥበትን አሰራር መዘርጋቱን ነው ጽ/ቤቱ ያስታወቀዉ፡፡
ሁልጊዜም የአገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል የሚተጋዉ እና ህዝብን አዳምጦ ምላሽ መስጠትን የትኩረት ማእከሉ ያደረገዉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በከንቲባ ፅ/ቤት በሚስጥር ጥቆማ የሚሰጥበትን ነፃ የጥሪ ማእከል 9977 ፣ የሚስጥር ሳጥንን ጨምሮ በተጨባጭ ቅሬታዉን በአካል ለበላይ አመራር ማቅረብ የሚችልበትን አሰራር የፊታችን ሐሙስ ጀምሮ ወደ ተግባር እንደሚገባ ገልጿል፡፡
በመሆኑም ከመጪዉ ሐሙስ ህዳር 25/2018 ጀምሮ ጠዋት ከ 2 ሰአት እስከ 7 ሰአት ድረስ ከገቢዎች ጋር ብቻ የተያያዘን ቅሬታ አመራሩ ተቀብሎ የሚስተናግድ መሆኑን በመረዳት በከንቲባ ፅ/ቤት ተጨባጭ ቅሬታ ያላቸዉ ማቅረብ የሚችሉ መሆኑን የከተማዉ አስተዳደሩ አሳዉቋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ለቀልጣፋ እና ፍትኃዊ አገልግሎት እንደሚተጋ ጨምሮ ገልጿል፡፡