በ2ዐኛው የብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በዓል ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ማንኛውንም ፈተና ወደ ድል በመቀየር የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማረጋገጥ በጋራ ልንረባረብ ይገባል ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ የጀመረችውን የብልጽግና ጉዞ ማንም ሊያስቆማት አይችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያጋጥሙን ትንኮሳዎችና ፈተናዎች ሳይበግሩን የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያዊያን ለአፍሪካውያን ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን የብልጽግና ምልክት እና ምሳሌ ለመሆን በትጋትና በትብብር መስራት ይገባናልም ብለዋል፡፡
በባዳ የተጠለፈ ገመድ እንዳይጠልፈን እርስ በርስ በመተሳሰብ እና በመተጋገዝ ቀልብ ገዝተን በንግግር ችግሮቻችንን በመፍታት ሰላማችንን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥተን ልንሰራ ይገባል፡፡
ሌብነትን በመጸየፍ የሀገር ክብርና የሕዝቦችን ጥቅም በማስቀደም ለዘመናዊነት እና ለለውጥ በተሰማራንበት የሥራ መስክ ሁሉ በትጋት መስራት ከሁሉም ይጠበቃል ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡