AMN ሕዳር 30/2018 ዓ.ም
የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ለፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ደኅንነት አገልግሎት የሚውል የሩት ሰርተፊኬት አገልግሎት አስጀምሯል፡፡
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ስርዓቱ አስተማማኝ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ እና ከጥቃት የተጠበቀ መሆኑን ለማረጋገጥ የሚውሉ ዲጂታል ሰርተፊኬቶችን ለማምረት የሚውል የሩት ሰርተፊኬት መሰጠት መጀመሩን በማስመልከት ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
በመግለጫው ላይ የተገኙት የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ትዕግስት ሀሚድ ኢትዮጵያ የዲጂታል 2025 ስትራቴጂን በማገባደድ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን መጀመሩዋን ገልጸዋል።

የሕዝብ አገልግሎቶች፣ የፋይናንስ ተሳትፎ እና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች በታመኑ ዲጂታል ስርዓቶች የሚከናወኑበትን እድል እየፈጠረ ይገኛልም ብለዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሯ አያይዘውም ለፋይዳ መታወቂያ ደህንነት የሚውል የዲጂታል ሰርተፊኬት አገልግሎት መጀመሩ ኢትዮጵያ ለእያንዳንዱ ዜጋ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ እምነት የሚጣልበት እና ሁሉን አቀፍ የዲጂታል አገልግሎቶችን ለመስጠት ያላትን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተናግረዋል፡፡
የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮዳሔ አርአያስላሴ በበኩላቸው፣ አገልግሎቱ ክፍተኛ ቁጥጥር የሚደረግበት እና የደህንነት ማስጠበቂያ ዲጂታል ቁልፎች የሚፈጠሩበት እንዲሁም የሚንቀሳቀሱበት መሆኑን አስረድተዋል።

እነዚህ ቁልፎች በዲጂታል መታወቂያው ላይ ያለውን የማንነት መረጃ ለመጠበቅ ጥቅም ላይ የሚውል የመተማመኛ ዲጂታል ፊርማ ለማዘጋጀት ይጠቅማሉ ብለዋል፡፡
የማንነት ስርቆትን መከላከል፡ ትክክለኛ ግለሰብን የማስመሰል፣ የማጭበርበር እና የማንነት መረጃን አላግባብ መጠቀምን ለመከላከል ይረዳል ብለዋል ።
ይህም የሀገራችንን ዲጂታል ምህዳር ተዓማኒነት ለማጠናከር እና የዜጎችን የዕለት ተእለት ሕይወት የሚደግፉ ዲጂታል አገልግሎቶችን አስተማማኝ መሠረት ለመገንባት ወሳኝ መሆኑን አቶ ዮዳሔ ገልፀዋል፡፡
በታምሩ ደምሴ