95 በመቶ የሚሆኑ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተጓዦች የሚያቋርጡት የቦሌ አለም ዓቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ፕላቲኒየም ደረጃ ያለው ፕሪሚየም ላውንጅ አስመርቋል።
አዲሱ ላውንጅ ለታማኝ ደንበኞቹ ፕሪሚየር አገልግሎት የሚሰጥበት መሆኑን የገለፁት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው 16 የተለያዩ አገልግሎት የሚሰጡ ክፍሎችን የያዘ መሆኑንም ገልፀዋል።
አየር መንገዱ የብር እና የወርቅ ደረጃ ያላቸው ላውንጆች ያሉት ሲሆን ዛሬ ያስመረቀው ፕሪሚየር ላውንጅ በአንድ ጊዜ ለአንድ ሺህ ተጓዦቹ ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት የሚስችል ስለመሆኑም ተነግሯል።

በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥና የአየር መንገዱ የቦርድ ሰብሳቢ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ ተቋሙ ለደንበኞቹ ክብር እንደሚሰጥ ማሳያ ነው ብለዋል።
አየር መንገዱ ኢትዮጵያ ከገነባቻቸው ስመጥር ብርቅዬ ተቋማት መካከል አንዱ ነው ያሉት የአየር መንገዱ የቦርድ ሰብሳቢ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ የበለጠ ስሙን ከፍ የሚያደርጉ መሰረተ ልማቶችን እየገነባ ነው ብለዋል።
በአሰግድ ኪዳነማሪያም