የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ ባለፉት አምስት ወራት የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ባከናወናቸው የሪፎርም ስራዎች፣ የስነ-ምግባር ጉድለት ባለባቸው 179 አመራሮችና ባለሙያዎች ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታወቀ።
የቢሮው የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ ለኤ ኤም ኤን ዲጂታል እንደገለጹት፣ ቢሮው የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት ባለፉት አምስት ወራት ሰፋፊ የአደረጃጀት፣ የቴክኖሎጂ እና የሰው ሀብት ልማት ስራዎች አከናውኗል ።
ቢሮው በዘረጋው የአሰራር ማሻሻያ ለብልሹ አሰራር በር የሚከፍቱና ለውሳኔ አሻሚ የሆኑ አሰራሮችን ለማስቀረት 24 አዳዲስ አሰራሮች ተዘርግተው ወደ ተግባር ገብተዋል ብለዋል ።
የዲጂታል ኢኮኖሚውን ውጥንን ለማሳካትና የግብር አሰባሰቡን ለማዘመን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች በውስጥና በውጭ አቅም እንዲለሙ መደረጋቸውንም አስረድተዋል።

በተለይም የቁጥጥር ስራውን በካሜራ ቴክኖሎጂ የታገዘ በማድረግ ግልጽነትን ለመፍጠር ጥረት መደረጉን ተናግረዋል።
ሰራተኛው የአገልጋይነት ስብዕና እንዲላበስና ለግብር ከፋዮች ተገቢውን ክብር እንዲሰጥ የአመለካከትና የክህሎት ስልጠናዎች መሰጠታቸውን ገልጸዋል።
ዳይሬክተሩ አጽንኦት ሰጥተው እንደገለጹት፣ ተገቢውን አገልግሎት አለመስጠትና ተገልጋይን ማመናጨቅ የስነ-ምግባር ችግር በመሆኑ ይህንንም ለማረም የተጠያቂነት ስርዓት ተዘርግቷል ብለዋል።
በዚህ መሰረት ባለፉት አምስት ወራት ተገቢውን አገልግሎት ባለመስጠትና በተለያዩ የሥነ-ምግባር ግድፈቶች ውስጥ የተገኙ 179 አመራሮችና ባለሙያዎች ተጠያቂ መደረጋቸውን ተናግረዋል።
ተጠያቂ ከተደረጉት መካከል 20 የሚሆኑት በተለያየ ደረጃ የሚገኙ አመራሮች መሆናቸውን አስረድተዋል።
እነዚህ እርምጃዎች በዋነኝነት በፍትሐዊነት ገቢን ለመሰብሰብና ቢሮው ከብልሹ አሰራር በጸዳ መልኩ ለማደራጀት የሚረዱ መሆናቸውን አቶ ሰውነት አየለ ከኤ ኤም ኤን ዲጂታል ገልፀዋል።
በሔለን ተስፋዬ