ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ዶ/ር ዛሬ የኢትዮ ጅቡቲ ምድር ባቡር አ.ማ ጉብኝት ማድረጋቸውን ገለፁ።
ጉብኝቱ የሀገራችንን ብሔራዊ የሎጂስቲክስ ክዋኔ ዐቅም ለመገምገም እና የሀገሪቱን እያደገ ያለ የልማት አጀንዳ ለመደገፍ በሎጂስቲክስ ዝግጁነት ላይ ገንቢ ውይይቶችን ለማካሄድ ጠቃሚ ዕድል ሰጥቶናል ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልፀዋል።
ኢኮኖሚያችን እያደገ ሲሄድ የሎጂስቲክስ ዘርፉ ካልዘመነ ዘላቂ ዕድገትን የሚገድብ ዋና መሰናክል መሆኑን ይቀጥላል ብለዋል።
አሁን በተለይ በውስጣዊ እና በራስ ዐቅም የባቡር መንገድ ግንባታ ላይ የተመዘገበው ዕድገት እጅግ የሚያስደንቅ መሆኑን አመላክተዋል።

ይህም የሀገር ውስጥ ዐቅምን ለመገንባት፣ ውጤታማነትን ለማሻሻል እና በባቡር ዘርፍ ውስጥ ረጅም ጊዜ የሚቆይ ዘላቂነትን ለማረጋገጥ ያለንን ጽኑ ቁርጠኝነትን እንደሚሳይ ተናግረዋል።
ሎጂስቲክስ ከባሕር እስከ መጋዘኖች ድረስ ያለውን ሙሉ ሰንሰለት እንደሚያካትት ገልጸዋል።
ይህም ወደቦች፣ የባቡር መንገዶች፣ አውራ ጎዳናዎች፣ የትራንስፖርት አገልግሎቶች እና የማከማቻ ተቋማትን ይጨምራል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅትም በእጃችን ውስጥ ባሉ መስኮች ላይ እንደ ደረቅ ወደቦች፣ የባቡር መሠረተ ልማት፣ አውራ ጎዳናዎች እና የመጋዘን ግንባታ አስፈላጊ ማሻሻያዎችና ዘመናዊ የማድርግ ሥራዎች በሂደት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል።
እነዚህን ተያያዥ የሎጂስቲክስ ክፍተቶችን በተቀናጀ መንገድ መፍታት የዘርፉን መሰናክሎች ለመሻር እና የሀገሪቱን ሰፊ የልማት ግቦች ለመደገፍ ወሳኝ ይሆናል ብለዋል።