የአዲስ አበባ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የ2018 የሐጅ ጉዞን አስመልክቶ ከከተማዋ የመስጅድ ኢማሞች እና ኮሚቴዎች ጋር የውይይት መርሃ ግብር ተካሂዷል።
የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሸይኽ ሱልጣን አማን ኤባ በዘንድሮው ዓመት የሳውዲ አረቢያ የሐጅ ሚኒስቴር ባወጣው መመሪያ መሰረት የሐጅ ምዝገባ በወቅቱ እንዲጠናቀቅ በመወሰኑ ህዝበ ሙስሊሙ ሳይዘናጋ በወቅቱ ምዝገባውን እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
በዚህም የመስጅድ ኢማሞች ፣ ኡለማዎች እንዲሁም አቅም እና ንያ ያላቸው ሙስሊሞች በተቀመጠው ጊዜ መሰረት የሐጅ ምዝገባ እንዲያከናውኑ በየመስጂዱ ጥሪ ሊያደርጉ እንደሚገባ ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የኢስላማዊ ተቋማት ተጠሪ ኡስታዝ አዩብ ደርባቸው በበኩላቸው የዘንድሮው የሐጅ ምዝገባ ከተቀመጠው የጊዜ ገደብ አንድም ቀን እንደማይጨምር አንስተው በጊዜ ምዝገባው ይደረግ ዘንድ የመስጅድ ኢማሞች እና ኡለሞች በተለያዩ መንገዶች ለህብረተሰቡ እንዲያደርሱ ጠይቀዋል።
ህዳር 22 የተጀመረው የዘንድሮው ዓመት የሐጅ ጉዞ ምዝገባ ጥር 18/2018 እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል።
በመሀመድኑር ዓሊ