የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ሃይማኖት ዘለቀ ሹመትን አጽድቋል።
ምክር ቤቱ 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ስብሰባውን ዛሬ አካሂዷል።
ምክር ቤቱ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ወይዘሮ ሃይማኖት ዘለቀ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣንን በዋና ዳይሬክተርነት እንዲመሩ የቀረበውን ረቂቅ መርምሮ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡
ወይዘሮ ኃይማኖት ዘለቀ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከሪፖርተርነት እስከ አርታኢነት እንዲሁም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) በሙያቸው አገልግለዋል፡፡
በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስራ አስኪያጅ ጽህፈት ቤት በምክትል ቢሮ ሀላፊ ማዕረግ የኮሙኒኬሽን ዘርፍ ሀላፊ በመሆን ማገልገላቸው ተገልጿል፡፡
እንዲሁም በቀድሞ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት በመስራት ሀገራቸውን አገልግለዋል፡፡