51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ(PRC) መደበኛ ስብሰባው ከጥር 4 እስከ 22 ቀን 2018 ዓ.ም የህብረቱ ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል።
ስብሰባው “ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል የአፍሪካ ህብረት ባዘጋጀው የ2026 መሪ ሃሳብ የሚካሄድ ነው።
የዘንድሮው መሪ ሀሳብ ጭብጥ በአፍሪካ የውሃ ደህንነትና ንጽህና አጠባበቅ ላይ ያተኮረ ነው።
በስብሰባው የሕብረቱ ተቋማት አመራሮች፣ የሕብረቱ አባል ሀገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች እንደሚሳተፉበት ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ስብሰባው የካቲት 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ እንዲሁም የካቲት 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚከናወነው 39ኛው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚቀርቡ ረቂቅ አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል።
በተጨማሪም ኮሚቴው በአፍሪካ ሕብረት ስር የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን የአፈጻጸም እንዲሁም ሕብረቱ እ.አ.አ በ2025 ያካሄዳቸውን ስብሰባዎች የተመለከቱ ሪፖርቶችን ያደምጣል።
ሰላም እና ደህንነት፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን ጨምሮ የኢኮኖሚ ትስስር፣ የተቋማዊ ሪፎርሞች እና የበጀት እቅዶችን የተመለከቱ የቴክኒክ ሰነዶችንም ያዘጋጃል።
ኮሚቴው በ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ሀሳብ ላይ ምክረ ሀሳቦችን ያቀርባል ተብሎ ይጠበቃል።
የኮሚቴው መደበኛ ስብሰባ ለዋናው ጉባኤ እንደ ይፋዊ የዝግጅት ስብሰባ የሚያገለግል ነው።
የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ የሕብረቱን ቋሚ ተወካዮችና የአባል ሀገራቱን አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ያቀፈ ነው።