የአፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ የማግኘት የጋራ ፍላጎት ታሪካዊ ፍትህን የሚያሰፍን ነው

You are currently viewing የአፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ የማግኘት የጋራ ፍላጎት ታሪካዊ ፍትህን የሚያሰፍን ነው
  • Post category:አፍሪካ

AMN ጥር 19/2018

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ አባል የመሆን የጋራ መሻት ታሪካዊ ፍትህን ማስፈንና እኩልነትን ማረጋገጥ እንደሚያስችል የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ።

አፍሪካ ለዘመናት ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ የምክር ቤቱን ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው ሲሉም ተናግረዋል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ከፍተኛ ደረጃ የህዝብ የክርክር መድረክ ትላንት ማምሻውን አድርጓል።

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት በበይነ መረብ ባደረጉት ንግግር አፍሪካ የዓለም ፈተናዎች በተናጠል እንደማይፈቱ በጽኑ ታምናለች ብለዋል።

ሊቀ መንበሩ ዓለም አቀፍ ህግ ከታሪክ ግንዛቤ ጋር በተሰናሰለ መልኩ መተግበር አለበት ያሉ ሲሆን በተለይም የቅኝ ግዛት እና የመዋቅራዊ ኢ-ፍትሃዊነት አሻራዎች የተለየ ትኩረት እንደሚያሻቸው አመልክተዋል።

ዩሱፍ አፍሪካ ለሰላም ያላት ቁርጠኝነት ተጨባጭ መሆኑን ገልጸው በሰላም አስከባሪ አስተዋጽኦዎች፣ የጸጥታ አካላት የህይወት መስዋዕትነቶችን በመክፈል፣ ከኃይል ይልቅ ለሕጋዊ ስርዓት መስፈን በቁርጠኝነት በመስራትና የአፍሪካ ህብረት ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጋር በሰላም ጉዳይ ያለውን ጠንካራ አጋርነት በማሳያነት ገልጸዋል።

አፍሪካ ለዓለም ሰላም እና ደህንነት መረጋጋጥ ብዙ ብታበረክትም አሁን በዓለም መድረክ ላይ ባላት ውክልና ላይ የኢ-ፍትሃዊነት ጉዳይ መሰረታዊ ችግር ሆኖ መቀጠሉንም ነው የተናገሩት።

55 ሀገራት እና 1 ነጥብ 4 ቢሊየን ህዝብ የያዘችው አፍሪካ 80 ዓመታትን ባስቆጠረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ አለማግኘቷ ኢ-ፍትሃዊ ብቻ ሳይሆን የምክር ቤቱን ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው ብለዋል።

የአፍሪካ የጋራ ፍላጎት በምክር ቤቱ ቋሚ ውክልና ከነሙሉ መብቶቿ ማግኘት ነው ያሉት ሊቀ መንበሩ ይህም እኩልነት፣ በዓለም ስርዓት ውስጥ ውጤታማነትና ታሪካዊ ፍትህ እንዲሰፍን ያደርጋል ሲሉ መግለጻቸውን ኤኤምኤን ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review