በሀገራዊ ምክክር መድረክ ሁሉም አሸናፊ ይሆናል ሲባል ምን ማለት ነው?

You are currently viewing በሀገራዊ ምክክር መድረክ ሁሉም አሸናፊ ይሆናል ሲባል ምን ማለት ነው?
  • Post category:ፖለቲካ

AMN ጥር 25/2018 ዓ.ም

ሀገራዊ ምክክር ባለድርሻ አካላትን (ባለ ደንታ አካላትን) በማሳተፍ ለሀገራቸው የሚበጀውን ሀሳብ እንዲያቀርቡ መደላድል የሚፈጥር ዲሞክራሲያዊ ሂደት ነው፡፡ በሥነ-ምክክር ዙሪያ የተዘጋጁ ልዩ ልዩ መዛግብት በሀገራዊ ምክክር ሂደቶች ሁሉም ባለድርሻ አካላት አሸናፊ እንደሚሆኑ ሲተነትኑ የሂደቱን የተለያዩ መገለጫዎች ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባል፡፡

ሂደቱ የተለያዩ የሃሳብ እና የፖለቲካ መሪዎች፣ የሕብረተሰብ ክፍሎች፣ መንግስት፣ ሲቪክ ማህበራት ወ.ዘ.ተ በልዩነቶቻቸው ላይ በመነጋገር የጋራ ጥቅም ሊያስገኙላቸው የሚችሉ የጋራ የመፍትሔ ሀሳቦችን ለማግኘት ጥረት ያደርጋሉ ፡፡

ይህ ሂደት ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርገው እንዴት እንደሆነ ከዚህ እንደሚከተለው ለማሳየት እንሞክራለን።

1. ሁሉን አካታች የሆነ ተሳትፎ እንዲኖር ማስቻሉ፤

የሀገራዊ ምክክር ሂደት ሁሉንም ባለድርሻ (ባለ ደንታ) አካላት በማሳተፍ ድምፆች በእኩል ደረጃ እንዲሰሙ መድረኩን ያመቻቻል፡፡ ይህም የዜጎች እና ባለድርሻ አካላትን እኩልነት በማረጋገጥ በሂደቱ አሸናፊ እንዲሆኑ ያስችላቸዋል፡፡

2. ሰላማዊ የልዩነት እና የግጭት አፈታት ዘዴ መሆኑ፤

ሂደቱ ከአሸናፊነት፣ ተሸናፊነትና ፊክክር መንፈስ በመውጣት ለጋራ ሀገር የጋራ አቅጣጫንና መፍትሔን በማበጀት ረገድ ትልቅ ሚናን ይጫወታል፡፡ ከዚህ አኳያ በጦርነት የሚመጣውን ውድመት ከማስቀረት ባሻገር ቁስል፣ ቁርሾ እና ጥላቻ የሚያመጣውን የአሸናፊ-ተሸናፊ ስነ-ልቦናን በማስወገድ ሁሉም ከሂደቱ አትራፊ እና ተጠቃሚ ሆኖ እንዲወጣ ያስችላል፡፡

3. በመተማመን ላይ የተመሰረተ ዘላቂ ሰላምን ማስፈኑ፤

በሀገራዊ ምክክር ሂደት ባለድርሻ አካላት ሀሳባቸውን፣ ምኞታቸውን፣ ልዩነታቸውን እንዲሁም ስጋታቸውን ተቀራርበው በነፃነት ሲገልፁ እርስ በእርስ ለመነጋገር፣ አንዱ ለሌላው ሀዘኔታንና ርህራሄን ለማሳየት ብሎም መተማመንን ለመገንባት አጋጣሚውን ይፈጥራሉ፡፡ ይህም አንዱ ሌላውን ከመፈረጅ ወይም ከመኮነን ይልቅ በመተማመንን ሁሉም ስለሀገራቸው ሰላም ዘብ እንዲቆሙ ያስችላል፡፡ ያንን ተከትሎም ሂደቱ ሁሉም የአሸናፊነትን መንፈስን እንዲጎናፀፍ መንገዱን ያመቻቻል፡፡

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review