AMN ጥር 27/2018 ዓ.ም
የአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት ዛሬ የሀገርና የትውልድ ገንቢ ለሆኑት መምህራኖቻችን የምስራች ቀን ነው ብለዋል፡፡
በ57 ሕጋዊ ሰውነት ባላቸው ማህበራት ተደራጅተው፣ የሚጠበቅባቸውን 25 በመቶ ቅድመ ቁጠባ ወደ 4 ቢሊዮን ብር ገደማ ለቆጠቡ 6,194 መምህራን፣ ከሊዝ ነፃ የለማ መሬት በማቅረብና የፋይናንስ አማራጮችን በማመቻቸት የመኖሪያ ቤት ግንባታን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረናል።
በዚህም መምህራኑ 25 በመቶ በመቆጠባቸውና ቀሪው 75 በመቶ ከባንኮች ጋር የፋይናንስ አማራጭ እንዲመቻች በማድረግ፣ ወቅታዊ አማካይ የሊዝ ዋጋው 24 ቢሊዮን ብር የሚገመት 40 ሄክታር መሬት በነፃ ቀርቧል ብለዋል፡፡
በተጨማሪም መንግስት ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ የካሳ ወጪ በመሸፈን፣ መምህራንን በማህበር በማደራጀት፣ የዲዛይን ስራዎችን በማከናወንና ኮንትራክተሮችን በመለየት አስፈላጊውን ድጋፍ አድርጓል። በዚህም ለመምህራን ያለንን ክብር በተግባር አሳይተናል።
መምህራንም ድርሻቸውን ተወጥተው ዛሬ የሳይት ዕጣ አውጥተው ተረክበዋል።
ዛሬ ያስጀመርነው የመምህራን ማህበር ቤት ግንባታ ያለ ምንም መስተጓጎል በተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳ እንዲጠናቀቅ ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ ማድረጋችንን እንቀጥላለን። ከመምህራን በተጨማሪ የተደራጁ ሌሎች የመንግስት ሰራተኞችንም በርቱ ለማለት እወዳለሁ ብለዋል፡፡
በመጨረሻም “አይቻልም፣ አይሳካም” ለሚሉ አስተሳሰቦች ቦታ ሳትሰጡ፣ በፍጥነት ተደራጅታችሁ በመቆጥብ ፋና ወጊ ለሆናችሁት መምህራን እንኳን ደስ አላችሁ እያልኩ፤ ለቤቶቹ ምረቃ እንደምንገናኝ ሙሉ እምነት አለኝ ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡