በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ የሚጠበቁ ጨዋታዎች

You are currently viewing በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ የሚጠበቁ ጨዋታዎች

AMN ጥር 29 ቀን 2018 ዓ.ም

የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐግብር ዛሬም ሲቀጥል ሰባት ጨዋታዎች ይከናወናሉ።

ማይክል ካሪክን በአሰልጣኝነት ከሾመ በኋላ ሦስት ተከታታይ ድል የቀናው ማንችስተር ዩናይትድ በሜዳው ኦልድትራፎርድ ቶተንሃም ሆትስፐርስን ይገጥማል።

ሁለቱ ክለቦች ለዓመታት የሊጉ ደረጃ ያሳደጉ ድንቅ ፍልሚያዎችን አድርገዋል። ግንኙነታቸው በአብዛኛው በዩናይትድ የበላይነት ቢጠናቀቅም በቅርብ ዓመታት ግን ቶተንሃም የሚያሸንፋቸው ጨዋታዎች በርክተዋል።

በተለያ 2024/25 የውድድር ዓመት ቶተንሃም ዩናይትድ ላይ ፍፁም የበላይነት የወሰደበት ነበር። የሰሜን ለንደኑ ክለብ በሊጉ ሁለት ጊዜ ፣ በካራባኦ ካፕ እና በዩሮፓ ሊግ ፍፃሜ በአራት አጋጣሚ ማንችስተር ዩናይትድን አሸንፏል።

በቶማስ ፍራንክ የሚመራው ቶተንሃም በሁሉም ውድድር ከማንችስተር ዩናይትድ ጋር ባደረጋቸው ስምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች አንድም ሽንፈት አልተመዘገበበትም።

ማንችስተር ዩናይትድ ለመጨረሻ ጊዜ ቶተንሃምን ማሸነፍ የቻለው በ2022/23 የውድድር ዓመት በኦልድትራፎርድ 2ለ0 የረታበት ነው።

የዛሬው ተጠባቂ ጨዋታ ለሁለቱም ክለቦች ሦስት ነጥቡ ያስፈልጋቸዋል። ዩናይትድ አሁን እያሳየ ያለውን ጥሩ ብቃት አስጠብቆ የቻምፒየንስ ሊግ ተሳታፊ ለመሆን ከጨዋታው ሙሉ ሦስት ነጥብ ያስፈልገዋል።

ወጥነት የጎደለው ቶተንሃም ሆትሰፐርስ ከወራጅ ቀጠናው በዘጠኝ ነጥብ ብቻ እንደመራቁ ድል ካላደረገ አሰልጣኙ የበለጠ ጫና ውስጥ መግባታቸው አይቀርም።

ማይክል ኦሊቨር በዋና ዳኝነት የሚመሩት ተጠባቂው ጨዋታ ቀን 9:30 ላይ ይጀምራል።

ምሽት 12 ሰዓት አምስት ጨዋታዎች ሲከናወኑ የሊጉ መሪ አርሰናል ሰንደርላንድን የሚያስተናግድበት ጨዋታ ይጠበቃል።

ሊጉን ከስምንት ዓመታት በኋላ የተቀላቀለው ሰንደርላንድ አርሰናልን ነጥብ ካስጣሉ ክለቦች አንዱ ነው። በስታዲየም ኦፍ ላይት የተደረገው የሁለቱ ክለቦች የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ 2ለ2 መጠናቀቁ ይታወሳል።

ከ22 ዓመታት በኋላ የሊግ ዋንጫ የማንሳት እድሉ እየሰፋ የመጣው አርሰናል በሜዳው ኤምሬትስ የሚያደርገውን የዛሬ ጨዋታ ያሸንፋል የሚሉ ግምቶች በርካታ ናቸው።

መድፈኞቹ ድሉን ካሳኩ ነገ ከሊቨርፑል ከሚጫወተው ማንችስተር ሲቲ የሚኖራቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ ዘጠኝ ማስፋት ይችላሉ።

በተመሳሳይ 12 ሰዓት ቦርንማውዝ ከአስቶንቪላ ፣ ዎልቭስ ከቼልሲ ፣ ፉልሃም ከኤቨርተን እንዲሁም በርንሌይ ከዌስትሃም ዩናይትድ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ።

ምሽት 2:30 ኒውካስትል ዩናይትድ በሴንት ጀምስ ፓርክ ብሬንት ፎርድን የሚያስተናግድበት ጨዋታም ይጠበቃል።

በሸዋንግዛው ግርማ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review