AMN የካቲት 22/2018
ሁለተኛው የአፍሪካ መከላከያ ሚኒስትሮች ኮንፈረንስ “ከአኩሪ ታሪክ፣ ወደ ብሩህ አድማስ” በሚል መሪ ሀሳብ ተካሂዷል፡፡
በጉባኤው ላይ የተገኙት ሚኒስትሮችና ወታደራዊ መሪዎች እንዳሉት፤ የዓድዋ ድል ለአህጉራዊ አንድነትና ልማት ትልቅ ትምህርት የሚቀሰምበት መሆኑን አረጋግጠዋል።
የአህጉሪቷን ውስብስብ ስትራቴጂካዊ ሁኔታ ለመቋቋም ወታደራዊ ትብብርን ማጠናከር፣ መረጃ መለዋወጥና ጥረቶችን ማቀናጀት ወሳኝ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡
የኬንያ መከላከያ ሚኒስትር ሶልፐን ቱያ እንዳሉት፤ የዓድዋ ድል የኢትዮጵያ ታሪክ ብቻ ሳይሆን የመላው ጥቁር ሕዝብ የማንነትና የነፃነት አርማ ነው፡፡
ድሉ በአውሮፓውያን የቅኝ አገዛዝ ቀንበር ስር ለነበሩ አፍሪካውያን የይቻላል የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀና ለፓን-አፍሪካዊነት እንቅስቃሴ መሠረት የጣለ ታላቅ ክስተት መሆኑን ተናግረዋል።
የደቡብ ሱዳን የመከላከያ እና የቀድሞ የጦር አርበኞች ጉዳይ ሚኒስትር ሌተናል ጄነራል ቾል ቶን ባሎክ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከ130 ዓመታት በፊት በዓድዋ የሰው ልጅ እኩልነትን በተግባር ያሳየችበት ነው ብለዋል፡፡
ይህም ለአፍሪካ የነፃነት ንቅናቄ መሠረት መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካውያንን መንፈስና ጥንካሬ ዳግም የቀሰቀሰች ታሪካዊ ሀገር መሆኗንም አክለዋል።
የዚምባብዌ የመከላከያ ምክትል ሚኒስትር ብሪጋዴር ጄኔራል ሌቪ ማዪህሎሜ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ድሉን የተቀዳጀችው በማንም ድጋፍ ሳይሆን በአገራዊ አንድነቷ መሆኑ ለሌሎች አገራት ትልቅ ኩራት ነው።
የዛምቢያ መከላከያ ኃይል አዛዥ ጄኔራል ጆፍሪ ሲቶንጎ ዚዬሌ፤ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ድሉን ከዘመናዊው የልማት ጉዞ ጋር በማያያዝ እያሳየች ያለችው ስኬት የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ በኢነርጂ ዘርፍ መስፋፋት እና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ረገድ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አርአያ መሆኗን ገልጸዋል።
የዓድዋ ድል ትናንት ነፃነትን እንዳመጣ ሁሉ ዛሬ ደግሞ ለአፍሪካ ብልጽግና እና ሰላም መከበር እንደ ዋነኛ መነሳሻ ሊያገለግል እንደሚገባ በኮንፈረንሱ ላይ መገለጹን ኢዜአ ዘግቧል።