AMN – መጋቢት 05/2018 ዓ.ም
የአዲስ አበባ ከተማ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ አገልግሎቱን ይበልጥ ለማዘመን፣ በሰው ኃይል ግንባታና ምቹ የሥራ አካባቢን በመፍጠር ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑን አስታወቀ።
ኤጀንሲው ይህንን የገለጸው የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ ሠራተኞቹ ባዘጋጀው የዕውቅና መርሃ ግብር ላይ ነው።
በመርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ፤ ዘመናዊ ከተማን ለመገንባት ከመሠረተ ልማት ዝርጋታ ባሻገር አስተማማኝ የመረጃ ሥርዓት መዘርጋት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ሥርዓት የዘመናዊ ከተማ አስተዳደር መገለጫ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል።
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ንጉሤ በበኩላቸው፣ በተቋሙ ባለፉት ሦስት ዓመታት በቴክኖሎጂ፣ በሰው ኃይል፣ በአሠራርና አደረጃጀት እንዲሁም ምቹ የሥራ አካባቢን በመፍጠር ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል።
ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ በዕለቱ ዕውቅና ለተሰጣቸው ሠራተኞች ባስተላለፉት መልዕክት፣ የተሰጣቸው ዕውቅና ወደፊት ለበለጠ ስኬት የሚተጉበት መሆን እንዳለበት አሳስበዋል።
ዕውቅና የተሰጣቸው የኤጀንሲው ሠራተኞች በሰጡት አስተያየት፣ የተደረገላቸው ዕውቅና ይበልጥ ተግተው እንዲሠሩ ትልቅ ዓቅም እንደሚፈጥርላቸው ገልጸዋል።
በመሀመድኑር ዓሊ