AMN- መጋቢት 28/2018 ዓ.ም
የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ በከተማዋ የምርት እጥረት እንዳይከሰትና የፍጆታ ዕቃዎች በበቂ ሁኔታ እንዲቀርቡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ ገልጸዋል።
የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና ለማቃለል ታስቦ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የተዘጋጀውን ባዛርና ኤግዚቢሽን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ መርቀው ከፍተዋል።
በወቅቱም የነዳጅ ዋጋ መጨመርን ተከትሎ ሊከሰት የሚችለውን የዋጋ ንረት ለመከላከል በ11ዱም ክፍለ ከተሞች ተመሳሳይ ባዛሮች መከፈታቸውን ተናግረዋል።
ይህም ነዋሪዎች ለምርት እጥረት እንዳይጋለጡና መሰረታዊ የፍጆታ ሸቀጦችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል።
የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ አድማሱ ደቻሳ በበኩላቸው፣ ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶች መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል፡፡

በዚህም በቂ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች ለህብረተሰቡ እንዲቀርቡ መደረጉን ነው ያነሱት።
ሸማቾች ካለምንም እንግልት ምርቶቹን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን በመግለፅም፣ ህብረተሰቡም የቀረበውን መልካም አጋጣሚ እንዲጠቀም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
በበየነ ታደሰ