የሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ ምሽት 12:30 ይጀምራል

You are currently viewing የሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ ምሽት 12:30 ይጀምራል

AMN – ነሃሴ 11/2017 ዓ.ም

አርብ ምሽት የተጀመረው የ2025/26 የውድድር ዓመት የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ ዛሬ ይከናወናል ።

ተከታታይ ዘጠኝ የውድድር ዓመት የመክፈቻ ጨዋታውን በኦልድትራፎርድ የሚያደርገው ማንችስተር ዩናይትድ አርሰናልን ያስተናግዳል ።

ዩናይትድ በተጠናቀቀው የ2024/25 የውድድር ዓመት በሊጉ ታሪክ አስከፊውን ውጤት አስመዝግቧል።

የ20 ጊዜ የሊጉ ሻምፒዮን ከዚህ ዝቅታ ለመውጣት ሦስት ወሳኝ የማጥቃት ሚና የሚወጡ ተጫዋቾችን አስፈርሟል።

ከ200 ሚሊየን ፓውንድ በላይ የወጣባቸው ማቴኡስ ኩኝሃ ፣ ብሪያን ምቤሞ እና ቤንጃሚን ሼሽኮ በሊጉ 44 ግብ ብቻ አስቆጥሮ 15ኛ ደረጃ ያጠናቀቀውን ክለብ ያሻሽላሉ ተብሎ ተስፋ ተጥሎባቸዋል ።

ቀያይ ሰይጣናቱ በመክፈቻ ጨዋታ ያላቸው ክብረወሰን ከየትኛውም ክለብ የተሻለ ነው ። ከ33 የፕሪሚየር ሊግ የመክፈቻ ጨዋታ 22ቱን አሸንፈዋል ።

ማንችስተር ዩናይትድ ዘንድሮ እስከ ስድስተኛ ደረጃ ከጨረሰ እንደ ስኬት ሊቆጠርለት ይችላል ።

ሦስት ተከታታይ የውድድር ዓመት ሁለተኛ ሆኖ ላጠናቀቀው አርሰናል ግን ዋንጫ ማንሳት እንደ ግዴታ ይቆጠራል።

መድፈኞቹ ከ22 ዓመት በኋላ የሊጉን ዋንጫ ለማሸነፍ ይረዱናል ያሏቸውን ተጫዋቾች አስፈርመዋል ።

በተለይ ቪክቶር ዮኬሬሽ እና ማርቲን ዙብሜንዲ የደጋፊውን ተስፋ ከፍ ያደረጉ ተጫዋቾች ናቸው።

ለአርሰናል የዘንድሮ የውድድር ዓመት 100ኛው ተከታታይ ተሳትፎው ነው ። በሊጉ ታሪክ ይህን የፈፀመ ሌላ ክለብ የለም ።

ይህን አስደናቂ ታሪካቸውንን በዋንጫ ለማጀብ ጉዞአቸውን በኦልድትራፎርድ ይጀምራሉ ።

መድፈኞቹ በኦልድትራፎርድ ያላቸው ክብረወሰን ግን የሚያኩራራ አይደለም ። ከ18 የመጨረሻ ጨዋታ በድል የተመለሱት በሁለቱ ብቻ ነው ። 10ጊዜ ተሸንፈው በስድስቱ አቻ ተለያይተዋል ።

ለአርሰናል ተስፋ የሚሰጣቸው ሁለቱ ድሎች የተመዘገቡት በአርቴታ ዘመን መሆኑ ነው ። የሰሜን ለንደኑ ክለብ ከሜዳው ውጪ ያለው ጥንካሬም ሌላ ተነሳሽነት ሊሰጠው ይችላል ።

የሚካኤል አርቴታው ቡድን በህዳር 2024 በኒውካስትል 1ለ0 ከተሸነፈ በኋላ ከሜዳ ውጪ ባደረጋቸው 14 ጨዋታዎች ሽንፈት አልተመዘገበበትም ።

ማንችስተር ዩናይትድ ከ አርሰናል እንደ ኦብታ ቁጥራዊ መረጃ 243 ጊዜ ተገናኝተዋል ። ዩናይትድ 99 ጊዜ በማሸነፍ የበላይ ሲሆን አርሰናል በ89ኙ ድል ቀንቶታል ።

ማንችስተር ዩናይትድ ዛሬ ካሸነፈ አርሰናልን በ100 ጨዋታ የረታ የመጀመሪያው ክለብ ይሆናል ።

ምሽት 12:30 የሚጀምረው ተጠባቂውን ጨዋታ ሳይመን ሁፐር በዋና ዳኝነት ይመሩታል ።

በሸዋንግዛው ግርማ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review