AMN – መጋቢት 10/2017
የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በሀገሪቱ የመጀመሪያ የሆነውን በወረቀት ሲስጥ የነበረውን የታካሚዎች የሜዲካል ቦርድ ወደ ዲጂታል ሰርተፍኬት በመቀየር አገልግሎት መስጠት ጀምሯል፡፡
በማስጀመሪያ መርሐ-ግብሩ፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ድጉማ የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የቦርድ ሰብሳቢ ባስተላለፉት መልዕክት ሆስፒታሉ የሀገሪቱ አንጋፋ ሆስፒታል መሆኑን አንስተዋል፡፡
በአሁን ሰዓት በሚሰጣቸው አገልግሎቶች ላይ እያመጣቸው ያሉ የሚታዩ በርካታ ለውጦች እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል፡፡
ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ህክምና ለሚፈልጉም የታካሚዎች እንግልት የሚቀንስ እና የአገልግሎት ፈላጊዎችን እርካታ የሚጨምር ዲጂታላይዝድ የሜዲካል ቦርድ ሰርተፊኬት መስጠት መጀመሩ የሆስፒታሉን የአገልግሎት አሰጣጥ ይበልጥ የሚያሻሽል እና አስመስለው የሚሰሩ ማስረጃዎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር አጋዥ እንደሆነ አመላክተዋል።
ዶክተር ደረጀ አክለውም የጤና ሚኒስቴር ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ህክምና ለሚፈልጉ ታካሚዎች ወጥ በሆነ አሰራር ማስተናገድ የሚያስችል መመሪያ እያዘጋጀ እንደሆነ ጠቁመው፣ ሆስፒታሉ ሁሉም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ ለማድረግ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክሮ እንዲቀጥሉ አሳስበው የጤና ሚኒስቴር ለሆስፒታሉ የሚያደርገውን ድጋፍ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።