ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የአሜሪካ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ እንዲሳተፉ ጥሪ አቀረቡ

You are currently viewing ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የአሜሪካ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ እንዲሳተፉ ጥሪ አቀረቡ

AMN ሰኔ 17/2017 ዓ.ም

ፕሬዝዳንት ታዬ በአንጎላ ሉዋንዳ እየተካሄደ ባለው ከአፍሪካ አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ ጎን ለጎን የአፍሪካና የአሜሪካ የግብርና የምግብ የቢዝነስ ዘርፍን ለማጠናከር ያለመ የፓናል ውይይት ላይ ተሳትፈዋል።

በፓናል ውይይቱ ከፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በተጨማሪ የኮት ዲቯር ጠቅላይ ሚኒስትር ሮቤርት ቡግሬ ማምቤና የኤስዋቲኒ ጠቅላይ ሚኒስትር ሩሴል ሚሶ ድላሚኒ ጨምሮ የአሜሪካና የአውሮፓና የአፍሪካ ኩባንያዎች ተዋካዮች ተሳትፈዋል።

ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ በፓናል ውይይቱ ባስተላለፉት መልዕክት አሜሪካ አሁን ላይ በአፍሪካ የምታደርገውን የኢንቨስትመንት ተሳትፎ ለማሳደግ ያላትን ፍላጎት አድንቀዋል።

አፍሪካ የአሜሪካ የኢንቨስትመንት መዳረሻ የሚሆን አቅም እንዳላት ጠቅሰው በአፍሪካ በኩል ሊለማ የሚችል መሬት፣ የሰው ሃብትና ትክክለኛ ፖሊሲ መኖሩን ማረጋገጥ ይገባል ማለታቸውን የኢዜአ ሪፖርተር ከስፍራው ዘግቧል።

በተለይም ጠንካራ የምግብ ሥርዓት መዘርጋት፣ አስተማመኝ የንግድ ትስስር መፍጠርና በምርቶች ላይ እሴት የሚጨምር ቀጣይነት ያለው ኢንቨስትመንት እንደሚያስፈልግ አጽንኦት ሰጥተዋል።

ከዚህ አኳያ የአሜሪካ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የግብርና ዘርፎች ለመሳተፍ የሚጋብዝ ከፍተኛ አቅም እንዳለ ተናግረው፤ ይህም በቅርቡ በተግባር ተፈትኖ የሚጨበጥ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል።

መግቢያ አፍሪካ አዲሲቷ ከፊት ተሰላፊ አህጉር እንኳ ባትሆን ለንግድና ኢንቨስትመንት ሥራ ምቹ ከሆኑ መዳረሻዎች መካከል ግን ናት። የአሜሪካ ባለሀብቶች ኢንቨስት እንድታደርጉ ጥሪ ስናደርግላችሁ በእኛ በኩል ሰፊና ለም የሚታረስ መሬት፣ እንዲሁም ወጣትና አምራች የሰው ሃይል፣ ትክክኛ ፖሊሲ እንዳለን አረጋግጥላችኋለሁ። ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥሪ የቀረበላቸው የአሜሪካ ኩባንያዎች ልብ ሊሉት የሚገባው ጉዳይ ከሁሉ ቀዳሚው ነገር ተፅዕኖን መቋቋም የሚችል የምግብ ስርዓት መገንባት መሆኑን ነው። በሁለተኛ ደረጃ ይበልጥ ጠንካራ የንግድ ትስስር መፍጠር እንዲሁም በሶስተኛ ደረጃ እሴት መጨመርን ማዕከል ያደረገ ዘላቂ ኢንቨስትመንትን ነው።

በኢትዮጵያ ለእርሻ ሥራ መዋል የሚችል ሰፊ ለም መሬት መኖሩን ጠቅሰው፤ ይህንን የግብርና ሥራ ሊያከናውን የሚችል ሰፊ የሰው ሃብት መኖሩንም ጠቅሰዋል።

እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ፤ አሁን ላይ ኢትዮጵያ በተለይም ከአፍሪካ ልማት ባንክ ጋር በመተባበር በተለይም በስንዴ ምርት ላይ በጥቂት ዓመት ውስጥ ከፍተኛ እመርታ ተመዝግቧል።

በመሆኑም የአሜሪካ የዘርፉ ተዋናዮች በኢትዮጵያ በተለይም በጥጥ ምርት፣ በአቮካዶና በስንዴ ምርት ላይ ቢሳተፉ ውጤታማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማረጋገጣቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

የአሜሪካ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የሚያደርጉት ኢንቨስትመንት ለረጅም ዓመት የሚዘልቅ መሆን እንዳለበት ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ አሳስበዋል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review