ሁለተኛው የንግድ ሳምንት ኤግዚቢሽን በኦሮሞ የባህል ማዕከል ተከፈተ

You are currently viewing ሁለተኛው የንግድ ሳምንት ኤግዚቢሽን በኦሮሞ የባህል ማዕከል ተከፈተ

AMN- ነሐሴ 19/2017 ዓ.ም

‎የኦሮሚያ ንግድ ቢሮ ያዘጋጀው ሁለተኛው የንግድ ሳምንት ኤግዚቢሽን በኦሮሞ የባህል ማዕከል ተከፍቷል፡፡

‎ከነሐሴ 19 እስከ 21/2017 ዓ.ም በሚቆየው በዚህ ኤግዚቢሽ ላይ የተለያዩ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች ቀርበዋል፡፡

‎”ሁሉን አቀፍ የንግድ ዕድገት ለብልጽግና ጉዞ ግብ” በሚል መሪ ሀሳብ በተከፈተው የኢትዮጵያን ይግዙ ኤግዚቢሽን ላይ ከሁሉም የኦሮሚያ ዞኖች የመጡ አምራቶች ምርትና አገልግሎታቸውን ይዘው ቀርበዋል።

‎ኤግዚቢሽኑን የከፈቱት የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር) ባደረጉት ንግግር፣ ገበያው እንዲረጋጋ፣ የኑሮ ውድነቱም እንዲቀንስ የኢትዮጵያን ይግዙ የንግድ ሳምንት መድረኮች ትልቅ ሚና እየተጫወቱ ነው ብለዋል።

‎መድረኩ ተኪ ምርትን በማበረታታትና ወጪ ምርትን በማሳደግ ረገድ ትልቃ ፋይዳ አለው ነው ያሉት።

‎የኦሮሚያ ክልል ንግድ ቢሮ ኃላፊ የሺ ጂማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ሳምንቱ የኦሮሚያ ክልል የንግድ ሳምንት ተብሎ መሰየሙን ጠቅሰው፣ ክልሉን ከሌሎች ክልሎች ጋር በንግድ ለማስተሳሰርና ልምድ እንዲለዋወጡ አላማ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

‎በክልሉ የሚመረቱ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በሚገባ ለማስተዋወቅ የሚያግዝ መድረክ ስለመሆኑም ነው የተናገሩት።

‎በኤግዚቢሽኑ ላይ ከቀረቡት ለዓለም ገበያ ከሚቀርቡ የግብርናና የማዕድን ምርቶች መካከል የቁም ከብቶችን ጨምሮ ቡና፣ ሰሊጥ፣ ማር እና ማሾ የተለያዩ የቦለቄ ዝርያዎች እና የአምቦ ድንጋይ ምርቶች የሚጠቀሱ ናቸው።

‎ለሀገር ውስጥ ገበያ ከሚቀርቡት ምርቶች ውስጥ ደግሞ የሰብልና የጥራጥሬ ምርቶች፣ ወተትና የወተት ተዋጽኦ፣ የስንዴ ዱቄት፣ የምግብ ዘይትና ሌሎች እሴት የተጨመረባቸው የፋብሪካ ውጤቶች ይጠቀሳሉ።

በምትኩ ተሾመ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review