የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ ከደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ማያርዲት ጋር የሁለቱን ሀገራት የኢኮኖሚ ትብብር ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ መክረዋል።
በገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ የተመራ ልዑክ ከኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተላከ መልዕክት ለፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር አድርሷል።
በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና በደቡብ ሱዳን የፋይናንስ ተቋማት መካከል ሊኖር ስለሚችል ትብብርም ውይይት መደረጉ ተጠቁሟል።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ኢኮኖሚያዊ ትስስሩን በሚያጠናክሩ በአየር ትራንስፖርት፣ በመሰረተ ልማት እና በነዳጅ ሃብት ጉዳዮች ላይ ጠቃሚ ውይይት ተደርጓል ብለዋል።
የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ለሕዝቦቻቸው የጋራ ጥቅም የሚረዳውን የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር ከፍተኛ ቁርጠኝነት እንዳላቸው ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በተያያዘ የቀጣናዊ ንግድን ለማሳዳግ የሚረዳውን ኢትዮጵያን፣ ደቡብ ሱዳንን እና ጂቡቲን የሚያገናኘው የንግድ እና ትራንስፖርት የኮሪደር ልማትን በተመለከተ ውይይት እንደተደረገበት ታውቋል።
የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤት ውይይቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማሳደግ የሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን አሳውቋል።
ሁለቱ አገሮች በክልሉ ዘላቂ ብልፅግናን ለማምጣት የኢኮኖሚ ውህደትን እና የመሠረተ ልማት ግንባታን ቅድሚያ እንደሚሰጡም የፕሬዚዳንቱ ጽህፈት ቤት ይፋ አድርጓል።