ሁለተኛውን ሀገር አቀፍ የኪነጥበብ ውድድር ከነሐሴ 28 እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ለማካሄድ ቅድመ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
የኪነጥበብ ውድድሩ ባለፉት ወራት በመላው የሀገሪቱ ክፍሎች ሲካሄድ እንደነበር የገለፁት የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነብዩ ባዬ (ረ/ፕ)፤ ከተሳታፊዎቹ የተጣሩ 364 የጥበብ ሰዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ በውድድሩ ተሳታፊ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።
ውድድሩ በሙዚቃ፣ በውዝዋዜ፣ በባህላዊ አልባሳት ፋሽን ሾው፣ በስዕል እና በመነባንብ ዘርፍ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር የሚካሄድ መሆኑንም ገልፀዋል። ለዚሁ ውድድር የሚሆኑ በሙያው ብቃት ያላቸው ዳኞች መሰየማቸውንም ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል።
ተወዳዳሪዎች ከመላው የኢትዮጵያ ክልሎች የተውጣጡ እንደመሆናቸው ህብረ-ኢትዮጵያዊነትን የሚያንፀባርቅ ውድድር ያካሂዳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ተጠቁሟል። ውድድሩ ሀገርና ጥበብ፤ ጥበብ ለኢትዮጵያ ማንሠራራት ብስራት በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄድ ይሆናል።
በአይናለም አባይነህ