AMN ሕዳር 28/2018 ዓም
አመራሩ የሚገጥሙ ተግዳሮቶችን ወደ ዕድል በመቀየር ለላቀ ስኬት መትጋት እንዳለበት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
“በመደመር መንግሥት ዕይታ፣ የዘርፎች እመርታ” በሚል መሪ ሀሳብ ለተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የቆየው 3ኛ ዙር የወረዳ አመራሮች ስልጠና ተጠናቋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማጠቃለያው ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት በሀገራችንና በመዲናዋ እየተመዘገቡ የሚገኙ ዘርፈ ብዙ ድሎች አመራሩ እና ሕዝቡ በቅንጅት ሰርተው ያሳኳቸው ናቸው ብለዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የስንዴ ልማትና የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በሀገራችንና በአዲስ አበባ የተመዘገቡ አስደናቂ ለውጦች ለበለጠ ሥራ የሚያነሳሱ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የአመራር ስልጠናው በአዲስ ዕይታ ለተጨማሪ ስኬት መትጋት የሚያስችል የእውቀትና የአመለካከት አቅም የተፈጠረበት እንደሆነም ገልጸዋል።

አመራሩ የሚገጥሙ ተግዳሮቶችን ወደ ዕድል በመቀየር ለላቀ ውጤት መትጋት እንዳለበት ያነሱት ከንቲባ አዳነች በሁሉም ዘርፍ አርዓያ ሊሆኑ የሚችሉ ሥራዎችን መሥራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል።
ለዚህም በማያቋርጥ የአመለካከት፣ የስነምግባርና የባህሪ ግንባታ ራስን ማብቃት አስፈላጊ መሆኑን አጽንዖት ሰጥተዋል።
ስልጠናው በግብርናና ገጠር ትራንስፎርሜሽን፣ በኢንዱስትሪ፣ በከተማ ልማትና በቱሪዝም ዘርፎች ላይ ያተኮረ መሆኑን አንስተው ስልጠናው በተሰናሰለ የዘርፎች እመርታ መዋቅራዊ ሽግግርንና ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማሳካት መግባባት የተፈጠረበት ነው ብለዋል።
ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተቀመጡ ሀገራዊ ግቦችን ለማሣካት አመራሩ በመፍጠርና መፍጠን መርህ መሥራት እንደሚጠበቅበትም
የከነቲባ ጽሕፈት ቤት ገልጿል።