የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት ዛሬ 3 ዘመናዊ ባለ 10 ወለል ስማርት የወረዳ የአስተዳደር ሕንፃዎችን ገንብተን ወደ ሥራ አስገብተናል ብለዋል፡፡
በከተማችን የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል ከተከናወኑ በርካታ ተግባራት መካከል አንዱ ለህዝብ ቅርብ የሆኑ የወረዳ አገልግሎት መስጫዎችን ማዘመን፣ በበቂ የሰው ኃይል ማደራጀት፣ በቴክኖሎጂ መደገፍ፣ እንዲሁም ለአገልግሎት ሰጪውና ለተገልጋዩ ማኅበረሰብ ምቹ የስራ ቦታን መፍጠር ይገኝበታል።
እነዚህ ስማርት የአስተዳደር ሕንፃዎች አገልግሎትን ወደ አንድ ማዕከል በመሰብሰብ፣ የተገልጋዩ ጊዜና ሀብት እንዳይባክን በማድረግ፣ እንግልትና ውጣ ውረድን በመቀነስ፣ በአንድ ማዕከል ፈጣንና ቀልጣፋ የወረዳ አገልግሎቶችን ማግኘት እንዲያስችሉ ተደርገው የተገነቡ ናቸው ብለዋል፡፡
ሕንፃዎቹ ዘመናዊ የመኪና ማቆሚያ፤ የልጆች ማቆያና መጫወቻ ስፍራ፤ ውብ፣ ጽዱና አረንጓዴ ቅጥር ጊቢ እንዲኖራቸው ተደርገው ተገንብተዋል። በተጨማሪም አካል ጉዳተኞችንና አቅመ ደካሞችን ታሳቢ ያደረጉ ሊፍቶች የተገጠሙላቸው ናቸው።
በመሆኑም ዛሬ በልደታ እና ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በሶስት ወረዳዎች ስራ ያስጀመርናቸው ባለ 10 ወለል ስማርት የአገልግሎት መስጫ የአስተዳደር ሕንፃዎች ከተማችንን ስማርት/ስሉጥ ከተማ ለማድረግ የጀመርነው ስራ አካል በመሆናቸው፣ በቀሪዎቹ ወረዳዎች ላይ የማስፋትና የማብዛት ሥራ በቀጣይም ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡