የኢትዮጵያና ሕንድ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የሀገሪቱን ዲፕሎማሲያዊ ተፈላጊነት እያሳደገ ነው

You are currently viewing የኢትዮጵያና ሕንድ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የሀገሪቱን ዲፕሎማሲያዊ ተፈላጊነት እያሳደገ ነው

AMN – ታኅሣሥ 10/2018 ዓ.ም

‎የኢትዮጵያና የሕንድ ስትራቴጂካዊ አጋርነት መጠናከር ሌሎች ሀገራት የኢትዮጵያን ተፈላጊነትና ቁልፍ ሚና እንዲገነዘቡ የሚያስችል መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ገለጹ።

‎አምባሳደሩ ከአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ የሁለቱ ሀገራት የቆየ ግንኙነት አሁን ላይ ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገሩንና ይህም የአፍሪካ-ሕንድ ግንኙነትን ወደ አዲስ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግር አስታውቀዋል።

‎ኢትዮጵያና ሕንድ ከሁለት ሺህ ዓመታት በላይ ያስቆጠረ የታሪክና የንግድ ትስስር ያላቸው ሲሆን፣ በዘመናዊ ዲፕሎማሲ ደግሞ ከ1948 ዓ.ም ጀምሮ ጠንካራ ወዳጅነት መስርተዋል።

‎ሕንድ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቁልፍ የልማት አጋር አድርጋ እንደምትመለከት የጠቀሱት አምባሳደሩ፣ ይህ ከልብ የመነጨ ወዳጅነት አሁን ላይ በግብርና፣ በማዕድን፣ በማኑፋክቸሪንግና በቴክኖሎጂ ዘርፎች ሰፊ ስትራቴጂካዊ ትብብር እየተፈጠረበት እንደሚገኝ ተናግረዋል።

‎ሁለቱ ሀገራት የብሪክስ (BRICS) አባል መሆናቸውና የጋራ የልማት ግቦችን መጋራታቸው፣ በዓለም ደቡባዊ ቀጣና (Global South) ውስጥ ያሉ ሀገራትን ተጽዕኖ ለማሳደግ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥርም ተገልጿል።

‎በተለይም እንደ ብድር ቅነሳ ያሉ ዓለም አቀፍ ተግዳሮቶችን ለመፍታትና የደቡብ-ደቡብ ትብብርን ለማጠናከር የሁለቱ ሀገራት ሚና ከፍተኛ አምባሳደር ዲና በአጽንዖት ተናግረዋል።

‎ሕንድ ለኢትዮጵያ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ዋና ምንጭ ከመሆኗም ባለፈ፣ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ባሉ መምህራን አማካኝነት የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ መጠናከሩንም ገልጸዋል።

‎የጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጉብኝትም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ተሰሚነት የሚያሳይና የኢኮኖሚ ትስስሩን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑንም ገልጸዋል።

‎በመጨረሻም፣ በሁለቱ ሀገራት መካከል የተደረጉ ስምምነቶች ተጨባጭ ፍሬ እንዲያፈሩ በትኩረት መተግበር እንደሚገባ አምባሳደሩ አሳስበዋል።

‎ ይህ በትኩረት የመስራት ልምድ ለወደፊቱ ተጨማሪ የኢንቨስትመንትና የልማት ስምምነቶች እንዲመጡ በር የሚከፍትና የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ እድገት የሚያፋጥን መሆኑንም ገልጸዋል።

በሄለን ጀንበሬ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review