የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ ማናቸው

You are currently viewing የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ ማናቸው

AMN – የካቲት 18/2018 ዓ.ም

የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ እ.ኤ.አ መስከረም 22 ቀን 1960 በእስራኤል የተወለዱ ሲሆን፣ የእስራኤል ስድስተኛ ፕሬዝዳንት የነበሩት የቻይም ሄርዞግ ልጅ ናቸው።

ሐምሌ 2021 የእስራኤል 11ኛው የእስራኤል ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙት አይዛክ ሄርዞግ ሀገራዊ አንድነትን የመጠበቅ እና እስራኤልን በዓለም አቀፍ መድረክ የመወከል ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል።

በዲፕሎማሲ እና በህዝብ አገልግሎት በታነጸ ቤተሰብ ውስጥ ያደጉት ሄርዞግ፤ ገና በለጋነታቸው የዓለም አቀፍ ጉዳዮች እና የመንግስት አስተዳደር ጥበብን ተለማምደዋል፡፡

አባታቸው በተባበሩት መንግስታት የእስራኤል አምባሳደር ሆነው በሰሩበት ወቅት የልጅነት ዘመናቸውን በከፊል በኒውዮርክ ያሳለፉ ሲሆን፣ ይህም የዓለም አቀፍ አመለካከታቸውን የቀረጸ ተሞክሮ ነበር።

በኒውዮርክ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ፣ ሄርዞግ በዩናይትድ ስቴትስ በሚገኙት ኮርኔል ዩኒቨርሲቲ እና ኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል።

በኋላም ወደ እስራኤል በመመለስ ከቴል አቪቭ ዩኒቨርሲቲ በህግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።

ይህም ለረጅም የፖለቲካ ዘመናቸው ደጋፊ የሚሆን ሙያዊ መሠረት ጥሎላቸዋል።

በእስራኤል መካከለኛ-ግራ ዘመም ፖለቲካ ውስጥ ዋነኛ ሰው የሆኑት ሄርዞግ፣ ከፈረንጆቹ 2003 እስከ 2018 ድረስ የክኔሴት (የእስራኤል ፓርላማ) አባል ሆነው አገልግለዋል።

በዚህ ጊዜ ውስጥ የማህበራዊ ደህንነት፣ የቱሪዝም እና የዲያስፖራ ጉዳዮችን ጨምሮ በርካታ ቁልፍ የሚኒስትርነት ቦታዎችን ይዘው ነበር።

በእነዚህ ሚናዎች የነበራቸው ቆይታ ለማህበራዊ ፍትህ፣ በውጭ ካሉ ማህበረሰቦች ጋር ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር እና እስራኤልን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማስተዋወቅ ትኩረት ሰጥተውበታል።

እ.ኤ.አ. በ2013 የሄርዞግ የእስራኤል ሌበር ፓርቲ ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠው፣ ፓርቲውን በወሳኝ የፖለቲካ ወቅት መርተዋል።

በሚዛናዊ ንግግራቸው እና በስምምነት ላይ በተመሰረተ አቀራረባቸው የሚታወቁት ሄርዞግ፣ በተለያዩ የፖለቲካ ልዩነቶች መካከል እንደ ድልድይ ሆነው ራሳቸውን አቅርበዋል።

እ.ኤ.አ. በ2021 ፕሬዝዳንትነቱን ከተረከቡ ጀምሮ፣ ሄርዞግ በእስራኤል ልዩ ልዩ ማህበረሰቦች መካከል አንድነት እንዲሰፍን ትኩረት ሰጥተው ሲሰሩ ቆይተዋል፤ የውጭ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችንም አስፍተዋል።

ከታዋቂ ስኬቶቻቸው መካከል ታሪካዊ ሀገራዊ ጉብኝቶች ይጠቀሳሉ፤ ለምሳሌ እ.ኤ.አ. በ2022 ወደ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ያደረጉት የመጀመሪያው የእስራኤል ፕሬዝዳንት ጉብኝት እና የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማደስ እና ለማጠናከር ወደ ቱርክ ያደረጉት ይፋዊ ጉብኝት ይጠቀሳሉ።

እነዚህን ሁሉ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎች የሰነቁት የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ በኢትዮጵያ እያደረጉት ያለዉ ጉብኝት፣ የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማጠናከር፣ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያለውን ትብብር ለማሳደግ እና በተለይም በምስራቅ አፍሪካ (የአፍሪካ ቀንድ) እና በቀይ ባህር አካባቢ ያሉ ወሳኝ ቀጣናዊ የጸጥታ ስጋቶችን ለመፍታት ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተብሎ ይታመናል።

በወንድማገኝ አሰፋ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review